የአገር ኅልውናን አደጋ ላይ ለመጣል የሚሠሩ ኃይሎችን በሕግ ተጠያቂ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠል የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አሳሰበ

12 Mons Ago
የአገር ኅልውናን አደጋ ላይ ለመጣል የሚሠሩ ኃይሎችን በሕግ ተጠያቂ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠል  የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አሳሰበ
የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ የአገር ኅልውናን አደጋ ላይ ለመጣል የሚሠሩ ኃይሎችን በሕግ ተጠያቂ የማድረግ ሥራ አጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ አሳሰበ።
ፈዴራል ፖሊስ በበኩሉ በቴክኖሎጂ የታገዘ የወንጀል መከላከል ሥራ እና ሕግ የሚተላለፉ አካላትን ተጠያቂ የማድረግ ሥራ ይቀጥላል ብሏል።
የኢትዮጵያ ፌዴራል ፓሊስ ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ ገብረሚካኤል፣ የተቋሙን የዘጠኝ ወራት አቅድ አፈፃፀም ሪፓርት በምክር ቤቱ ለሕግ እና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አቅርበዋል።
የቀረበውን ሪፖርት ተከትሎ የቋሚ ኮሚቴው አባላት ጥያቄ እና አስተያየቶችን ሰጥተዋል።
የሀገርን ሀብት እና ሉዓላዊነት አደጋ ላይ ለመጣል በተለያዩ አካላት የሚፈፀሙ ወንጀሎችን በመከላከል እና አጥፊዎችን በሕግ ተጠያቂ የማድረግ ሥራ ጥሩ ውጤት እየታየበት መሆኑን የቋሚ ኮሚቴው አባላት አንሥተዋል።
የኮንትሮባንድ ንግድ፣ ሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር እና ሕገ-ወጥ የመሣሪያ ዝውውርን በመከላከል ረገድም እንዲሁ።
የሕግ እና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወ/ሮ እፀገነት መንግሥቱ፣ ፌዴራል ፖሊስ የተለያዩ ወንጀሎችን በመከላከል ረገድ እያከናወናቸው ያሉ ሥራዎችን አድንቀዋል።
በቀጣይም የወንጀል መከላከል ሥራን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ታግዞ የማከናወን ሥራ ትኩረት ሊያደርግበት ይግባል ብለዋል።
ኮሚሽኑ የሚያከናውናቸውን ዘርፈ-ብዙ ሥራዎች በቴክኖሎጂ የታገዘ እንዲሆን ለማድረግ የሄደበት ርቀት የሚበረታ መሆኑንም ነው የገለጹት።
የኮንትሮባንድ ንግድ፣ ሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር እና ሕግ-ወጥ የመሣሪያ ዝውውርን መከላከል ላይ በቀጣይ ዋነኛ ትኩረቱ ማድረግ አለበት ብለዋል።
በተለይም የአገር ኅልውናን አደጋ ላይ ለመጣል የሚሠሩ ኃይሎችን የመለካለል እና በሕግ ተጠያቂ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ አሳስበዋል።
የኢትዮጵያ ፌዴራል ፓሊስ ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ ገብረሚካኤል በበኩላቸው፣ ተቋሙ በዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች በመታገዝ ወንጅሎችን የመከላከል እና አጥፊዎችን በሕግ ተጠያቂ የማድረግ ተግባሩን ቀጥሏል ብለዋል።
በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት በሕግ-ወጥ መንገድ ከአገር ሊወጡ የነበሩ 2 ሺህ 316 ሰዎች እንዲመለሱ መደረጉን እና በወንጀሉ የተሳተፉ 63 ተጠርጣሪዎችም በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ኮሚሽነር ጄኔራሉ ጠቅሰዋል።
በሕገ-ወጥ መንገድ ሲንቀሳቀስ የነበረ ከ1.1 ሚሊየን በላይ የውጭ አገር ገንዘብ ከወንጀሉ ተጠርጣሪዎች ጋር መያዙንም ገልጸዋል።
በመሆኑም በቀጣይ የወንጀል መከላከል ሥራዎችን እና አጥፊዎችን ተጠያቂ የማድረግ ሥራ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል።
የቋሚ ኮሚቴው አባላትም በጥሩ ጅምር ላይ ያሉ ሥራዎችን በማጠናከር የአገር ኅልውናን የማስጠበቅ እና ወንጀለኞችን በሕግ አግባብ ተጠያቂ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ማሳሰባቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

ተያያዥ ርዕሶች

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top