የፕሪቶሪያ ስምምነት መነሻና መድረሻው ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ተቋማትን ማክበር ነው! - የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

1 Mon Ago 338
የፕሪቶሪያ ስምምነት መነሻና መድረሻው ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ተቋማትን ማክበር ነው! - የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

የፕሪቶሪያ ስምምነት መነሻና መድረሻው ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ተቋማትን ማክበር ነው ሲል የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ገለፀ፡፡

ወቅታዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ከመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት የተሰጠው መግለጫ እንደሚከተለው ቀርቧል፦

የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ከሰሞኑ በተሻሻለው የምርጫ አዋጅ ቁጥር 1332/2016 አንቀጽ 2 (1) መሠረት ለሕወሐት የምዝገባ ምስክር ወረቀት መስጠቱን ገልጧል። መንግሥት ሕገ መንግሥታዊ ተቋማት በሕግና በተቋማዊ ነጻነት የሚወስኑትን ውሳኔ ይቀበላል። ያደንቃል። የለውጡ አንዱ ፍሬ ነውና።

ሕወሐት ሕጋዊ ሰውነቱን ያጣው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በፖለቲካ ፖርቲዎች የምዝገባ እና የሥነ ምግባር አዋጅ መሠረት ባስተላለፈው ውሳኔ መሆኑ ይታወሳል። ቦርዱ ፖርቲው በኃይል እና በዐመጽ እንቅስቃሴ በመሳተፉ የፓርቲውን ምዝገባ እንዲሠረዝ በመወሰኑ፣ ሕወሐት ሕጋዊ ሰውነቱን ማጣቱ ይታወቃል። ይህ የምርጫ ቦርድ ውሳኔ የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሕወሐትን ሽብርተኛ ብሎ ከመፈረጁ በፊት የተላለፈ እና ራሱን ችሎ የሚቆም፣ የራሱ የሕግ መሠረት ያለው ውሳኔ ነው።

የፕሪቶሪያ ስምምነት ሲፈጸም የፌዴራል መንግሥት በስምምነቱ የገባው ግዴታ የሕወሐት የሽብርተኝነት ፍረጃ እንዲነሣ ሂደቱን የማሣለጥ ኃላፊነት ነው (የስምምነቱ አንቀጽ 7 (2) (C)):: የፌዴራል መንግሥት የሕወሐትን የሕግ ሰውነት እና የምዝገባ ጉዳይ በተመለከተ በፕሪቶሪያ ስምምነት ውስጥ የወሰደው የተለየ ኃላፊነት ወይም ግዴታ አልነበረም። እንዲሁም ሕወሐት በፕሪቶሪያ ስምምነት አንቀጽ 7 (1) (A) መሠረት የሀገሪቱን ሕገ መንግሥት፣ ሕጎች፣ የፌዴራል ተቋማትን እና ሌሎች ሕገ መንግሥታዊ ተቋማትን ሥልጣን የማክበር ግዴታ ገብቷል። ስለዚህ ሕወሐት የሀገሪቱን የፖለቲካ ፖርቲዎች የምዝገባ ሕግ እና የምርጫ ቦርድን ሥልጣን በማክበር የመሥራት ግዴታ እንዳለበት ግልጽ ነው።

ስለሆነም፣ ከፕሪቶሪያ ስምምነት አኳያም ሲታይ የሕወሐት የሕግ ሰውነት ጉዳይ አግባብነት ባለው ሕግ እና በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አሠራር መሠረት ብቻ እልባት ሊያገኝ የሚገባ ጉዳይ ነው። የፌዴራል መንግሥት በዚህ ረገድ ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እና ከሕወሐት አመራሮች ጋር ተደጋጋሚ ምክክሮችን በማድረግ፣ ሕወሐት እንደ ፖለቲካ ፖርቲ ሕጋዊ ዕውቅና እንዲኖረው ሁኔታዎችን ለማመቻቸት ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል። በዚህ ረገድ የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አቋም፣ ሕወሐት ማንኛውም አዲስ የፖለቲካ ፖርቲ በሚመሠረትበት ሥርዓት እና አግባብ መሠረት እንደ አዲስ ፖርቲ በመደራጀት ሊመዘገብ እና ዕውቅና ሊያገኝ ይችላል፣ ከዚህ ውጪ ግን ሕጋዊ ሰውነት ሊያገኝ የሚችልበት ሕጋዊ አሠራር የለም የሚል ነበር። በሕወሐት በኩል የነበረው አቋም ነባር እና እድሜ ጠገብ የፖለቲካ ድርጅት ስለሆንኩኝ እንደ አዲስ ፓርቲ ልመዘገብ አይገባም፣ ጉዳዩ የሕግ ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ ስለሆነ የተለየ የፖለቲካ ውሳኔ ይፈልጋል የሚል ነው።

እነዚህን የተለያዩ አቋሞች እና ፍላጎቶችን ከግምት በማስገባት፣ ሰላምን የማጽናት አስፈላጊነትን፣ እንዲሁም የዴሞክራሲ ተቋማትን ነጻነት እና ገለልተኝነት ባገናዘበ መልኩ ለጉዳዩ እልባት ለመስጠት የተሻለው መንገድ፣ ሕውሐትም ሆነ ሌሎች የትጥቅ እንቅስቃሴ ላይ ያሉ ቡድኖች ወደ ሕጋዊ መሥመር ሊመጡ የሚችሉበትን መንገድ የሚያመቻች የሕግ ማሻሻያ ማድረግ እንደሆነ በፌዴራል መንግሥት በኩል ታምኖበት አስፈላጊው የሕግ ማሻሻያ ለሕዝብ ተወካዮች ቀርቦ ጸድቋል።

በዚህ መሠረት የኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነ ምግባር አዋጅ ከተሻሻለ በኋላ፣ በተሻሻለው የአዋጁ ድንጋጌ መሠረት ሕወሐት የሕግ ሰውነት እንዲያገኝ ለማድረግ አስፈላጊ ወይም ቅድመ ሁኔታ የሆነው የሰላም ስምምነት መፈጸምን አስመልክቶ የፍትሕ ሚኒስቴር ለምርጫ ቦርድ ድብዳቤ ጽፏል። በዚህም የሕወሐት ሕጋዊ ሰውነት ጉዳይ እልባት እንዲያገኝ ከመንግሥት በኩል ሊደረግ የሚችለው ሁሉ ተደርጓል። የፌዴራል መንግሥት ከግማሽ ርቅት በላይ ሄዶ፣ በፕሪቶሪያ ስምምነት መሠረት ከሚጠበቅበት እና ካለበት ግዴታ አልፎ ከምርጫ ቦርድ እና ከሕወሐት ጋር በጉዳዩ ላይ ተከታታይ ውይይቶች አድርጓል።

በተደረገው የሕግ ማሻሻያ መሠረት ምርጫ ቦርድ ሕወሐትን በመመዝገብ ድርጅቱ ሕጋዊ ሰውነት እና ዕውቅና እንዲኖረው ለቦርዱ የትብብር ጥያቄ አቅርቧል። ይህንንም ተከትሎ ሕወሐት ሕጋዊ ሰውነት እና ዕውቅና ለማግኘት የሚጠበቅበት የፓርቲ ሰነዶቹን ማለትም የፓርቲውን ፕሮግራም እና ሕገ ደንብ፣ እንዲሁም ሌሎች ተያያዥ ሰነዶችን ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በማቅረብ በተሻሻለው አዋጅ መሠረት ተመዝግቦ ሕጋዊ ሰውነት አግኝቷል።

ስለሆነም የምዝገባ እና የህግ ሰውነትን ጉዳይ በዚህ በመቋጨት፤ የሁሉም ባለድርሻ አካል ርብርብ፣ ሰላምን በማጽናት፣ በመልሶ ግንባታ እና በልማት አጀንዳ ላይ ሊሆን ይገባል። አላስፈላጊ እና ሕዝብን የማይጠቅም፣ ትርጉም አልባ ንትርክን አስወግደን ለሕዝብ ረብ ያላቸው ጉልህ የሰላም እና የልማት አጀንዳዎች ላይ ልናተኩር ይገባል።


አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top