በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ ሩብ ዓመት ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ከ271 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ መሰብሰቡን የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽህፈት ቤት ገለጸ።
የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በኢትዮጵያውያን የተባበረ ክንድ ወደ ማጠናቀቂያ ምዕራፍ ተሸጋግሯል።
የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽህፈት ቤት የፐብሊክ ዲፕሎማሲ ህዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ስራ አስፈጻሚ ሰለሞን ዳንኤል፤ በ2017 በጀት ዓመት ለህዳሴ ግድብ ግንባታ 1 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ድጋፍ ለመሰብሰብ መታቀዱን አውስተዋል።
በመጀመሪያው ሩብ ዓመት በሀገር ውስጥና በውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልድ ኢትዮጵያውያን በቦንድ ሽያጭ፣ በ8100 አጭር የፅሑፍ መልዕክትና በስጦታ ከ271 ሚሊየን ብር በላይ ድጋፍ መሰብሰቡን ተናግረዋል።
በዓመቱ የታቀደውን ድጋፍ ለማሰባሰብ በትኩረት ይሰራል ያሉት ስራ አስፈጻሚው፤ ህዝቡም እስከ ግንባታው ፍጻሜ ድጋፉን እንዲቀጥል ጥሪ ማቅረባቸውን ኢዜአ ዘግቧል።
መገናኛ ብዙሃንና እውቅ የማህበራዊ ሚዲያ አንቂዎች የገቢ ማሰባሰቢያ አማራጮችን ለህብረተሰቡ በማሳወቅ ሚናቸውን እንዲወጡም ጠይቀዋል።