በመዲናዋ ከየካቲት 3 እስከ 10 ቀን የሚደረጉ ኩነቶችን በስኬት ለማጠናቀቅ ግብረ ኃይሉ በፀጥታ ዕቅድ ላይ ተወያይቶ ወደ ስራ መግባቱን አስታወቀ

8 Mons Ago 398
በመዲናዋ ከየካቲት 3 እስከ 10 ቀን የሚደረጉ ኩነቶችን በስኬት ለማጠናቀቅ ግብረ ኃይሉ በፀጥታ ዕቅድ ላይ ተወያይቶ ወደ ስራ መግባቱን አስታወቀ

በአዲስ አበባ ከተማ ከየካቲት 3 እስከ 10 ቀን 2016 ዓ/ም የሚደረጉ ኩነቶችን በስኬት ለማጠናቀቅ የፀጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል በፀጥታ ዕቅድ ላይ ተወያይቶ ወደ ስራ መግባቱን አስታውቋል።

ግብረ ኃይሉ ባለድርሻ አካላት እና ህብረተሰቡ የተለመደ ትብብራቸውን እንዲያደርጉም ጠይቋል።

የካቲት 3 ቀን 2016 ዓ/ም ልዩ ልዩ እንግዶች እና የመንግስት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት የጋራ ትርክታችንን ይበልጥ የሚያጎላው የአድዋ መታሰቢያ ሙዚየም በደማቅ ስነ-ስርአት በልዩ ልዩ ዝግጅቶች ይመረቃል።

የምረቃ ስነ-ስርአቱ በሰላም እንዲከናወንም የፀጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል ጥር 27 ቀን 2016 ዓ/ም በአዲስ አበባ ፖሊስ ሠላም አዳራሽ ውይይት አድርጓል።

በዚህ ውይይት ላይ የሀገር መከላከያ፣ የፌዴራል ፖሊስ፣ የብሔራዊ መረጃ ደህንነት አገልግሎት፣ የአዲስ አበባ ከተማ ሠላምና ፀጥታ ቢሮ፣ የአዲስ አበባ ፖሊስ፣ የሸገር ከተማ ፖሊስ እና ሌሎች የፀጥታ አካላት ተሳትፈዋል።

ውይይቱን የመሩትና የስራ መመሪያ የሰጡት የፌደራል ፖሊስ ወንጀል መከላከል ዘርፍ ኃላፊ ምክትል ኮሚሽነር ጀነራል መላኩ ፋንታ ሲሆኑ፤ በመድረኩ የአዲስ አበባ ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ሊዲያ ግርማ እና የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው ተገኝተዋል፡፡

የካቲት 3 ቀን 2016 ዓ/ም የፌዴራል እና የአዲስ አበባ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች ፣ የውጭ ሀገራት እንግዶች ፣ ዲፕሎማቶች ፣ ታዋቂ ግለሰቦች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት የኢትዮጵያ ብሔር፤ ብሔረሰቦችና ህዝቦች የትስስር አርማ የመላው ጥቁር ህዝቦች የነፃነታቸው ብስራት የሆነው የአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም በደማቅ ስነ-ስርአት በልዩ ልዩ ዝግጅቶች ይመረቃል።

የምረቃ በዓሉን ተከትሎም በዕለቱ የትራፊክ መጨናነቅ  እንዳያጋጥም የተወሰኑ መንገዶች ለተሽከርካሪ ዝግ እንደሚሆኑም የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታውቋል፡፡ በዚህም መሰረት፡-

  • ከአፍንጮ በር ወደ ቅ/ጊዮርጊስ ቤ/ክርስቲያን
  • ከሰሜን ሆቴል ወደ ቅ/ጊዮርጊስ ቤ/ክርስቲያን
  • ከዮሃንስ ቤተ ክርስቲያን ወደ አቡነ ጴጥሮስ
  • ከአራት መንታ ወደ ጅንአድ
  • ከይርጋ ሃይሌ የገበያ ማዕከል ወደ አቡነ ጴጥሮስ
  • ከሃብተ ጊዮርጊስ ድልድይ ወደ ሱማሌ ተራ
  • ከሱማሌ ተራ ወደ ኤሊያና ሆቴል(ባንኮዲሮማ) መስቀለኛ
  • ከተክለ ሃይማኖት አደባባይ ወደ ቴዎድሮስ አደባባይ
  • ከአገር አስተዳደር መብራት( ኢሚግሬሽን) ወደ ቴዎድሮስ አደባባይ
  • ከንግድ ማተሚያ ቤት ወደ ቴዎድሮስ አደባባይ
  • ከአሮጌው ቄራ ወደ ባንኮ ዲሮማ መብራት
  • ከራስ መኮንን ድልድይ ወደ ደጎል አደባባይ
  • ከራስ መኮንን ድልድይ ወደ ቅ/ጊዮርጊስ ቤ/ክርስቲያን
  • ከመቅደላ ሆቴል ወደ ቅ/ጊዮርጊስ ቤ/ክርስቲያን
  • ከቅ/ጊዮርጊስ ቤ/ክርስቲያን ወደ ቴሌ እና ወደ ቅ/ጊዮርጊስ ቤ/ክርስቲያን ፊት ለፊት ወደሚገኘው አደባባይ የሚወስዱት መንገዶች የካቲት 3 ቀን 2016 ዓ/ም ከቀኑ 6 ሰዓት ጀምሮ ለተሽከርካሪ ዝግ ስለሚሆኑ አሽከርካሪዎች ይህንን ተገንዝበው አማራጭ መንገዶችን እንዲጠቀሙ እና የትራፊክ ፖሊሶች በሚጠቁሟቸው አማራጭ አቅጣጫዎችን በመጠቀም አስፈላጊውን ትብብር  እንዲያደርጉ የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታውቋል፡፡

በዋዜማው የካቲት 2 ቀን 2016 ዓ/ም ከላይ በተጠቀሱት መንገዶች እና የምረቃ ስነ ስርዓቱ በሚከናወንበት በአድዋ መታሰቢያ ሙዚየም ዙሪያ ተሽከርካሪ ማሳደርም ሆነ ለአጭርም ሆነ ለረጀም ሰዓት አቁሞ መሄድ የተከለከለ መሆኑንም አሳስቧል፡፡

ይለፍ ያላቸው አሽከርካሪዎች ቸርችር ጎዳና ጫፍ የቀድሞ ሜክሲኮ ታክሲ ተራ እና ከቴዎድሮስ አደባባይ እስከ ቸርችር ጎዳና ጫፍ መኪናዎቻቸውን መቆም እንደሚችሉ አዲስ አበባ ፖሊስ ገልፆ፤ ለጋራ ደህንነት ሲባል ፍተሻ እንደሚኖር የፕሮግሙ ታዳሚዎች ተገንዝበው የተለመደ ትብብር እንዲያደርጉ መልእክቱን አስተላልፏል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ የምረቃ ሥነ-ሥርዓት ተጀምሮ እሰከሚጠናቀቅ ጥሪ ከተደረገላቸው እንግዶች ውጪ ወደ አድዋ መታሰቢያ ሙዚየም የሚወስዱ መንገዶች ዝግጅቱ ተጀምሮ እስከሚጠናቀቅ ለእግረኞችም ዝግ መሆናቸውን አዲስ አበባ ፖሊስ  አስታውቋል፡፡


አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top