የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴዔታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ከሆኑት ኧርቪን ጆዝ ማሲንጋ ጋር ተወያይተዋል።
ውይይቱ በወቅታዊ የሁለትዮሽ፣ ቀጣናዊ እና የባለ ብዙ ወገን ጉዳዮች ላይ ያተኮረ እንደነበር ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
በሁለቱ አገራት መካከል ስላለው የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት እንዲሁም አገራቱ በተለይ በትምህርት፣ አቪዬሽን እና ንግድ ዘርፎች ስለሚያደርጉት ትብብር መክረዋል።
ኢትዮጵያ እና አሜሪካ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የመሰረቱበት 120ኛ ዓመት በቅርቡ እንደሚከበር የጠቀሱት አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ፤ ክብረ በዓሉ ሁለቱ አገራት ግንኙነታቸውን የሚገመግሙበትን እና ትብብራቸውን የሚያጠናክሩበትን ዕድል ይፈጥራል ብለዋል።
አምባሳደር ማሲንጋ በበኩላቸው የኢትዮ-አሜሪካ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት 120ኛ ዓመት ክብረ በዓል ሁለቱ አገራት በረጅሙ ታሪካዊ የሁለትዮሽ ግንኙነታቸው ያሳለፏቸውን ዋና ዋና ክስተቶች ለማጉላት መልካም አጋጣሚ ይሆናል ብለዋል።