የህጻን ሔቨን ጉዳይ እንዴት ተዳኘ?

2 Mons Ago 359
የህጻን ሔቨን ጉዳይ እንዴት ተዳኘ?

(በይፋ ከተዘገቡ እና ይፋ ካልሆኑ መረጃዎች አንፃር የተቃኘ)

. ክሱ ምን ይል ነበር?

የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የባህርዳር እና አካባቢዋ ከፍተኛ ፍ/ቤት፤ በምዕራብ ጎጃም ዞን አቃቤ ህግ መስከረም 19 ቀን 2016 ዓ.ም የ7 ዓመቷ ሔቨን አወትን አስገድዶ በመድፈር እና ወንጀሉን ለመደበቅ አንገቷን አንቆ ገድሏታል በሚለው ጌትነት ባይህ የተባለ ግለሰብ ላይ ሁለት የወንጀል ድንጋጌዎችን ጠቅሶ ክስ ያቀርብበታል።

የመጀመሪያው ክስ አስገድዶ መድፈርን የሚመለከተውን የወንጀል ሕጉን አንቀፅ 620(3) በመተላለፍ ማንም ሰው አንዲት ሴትን አስገድዶ በመድፈሩ ከባድ የአካል ወይም የአዕምሮ ጉዳትን ወይም ሞትን ያስከተለ ሲሆን ቅጣቱ እስከ ዕድሜ ልክ እሥራት እንደሚሆን በሚደነግገው አንቀፅ ስር የቀረበ ነው።

ሁለተኛው ደግሞ የአስገድዶ መድፈር ወንጀሉን ለመደበቅ ሲል ተከሳሽ ህፃን ሔቨንን አስገድዶ ከደፈራት በኋላ ወንጀሉ እንዳይታወቅበት እና አስቦ አንገቷን አንቆ ጨካኝ፣ ነውረኛ ወይም አደገኛ መሆኑን በሚገልፅ ሁኔታ በመግደሉ የወንጀል ሕግ አንቀፅ 539(1) (ሐ) በመተላለፍ ከባድ ግድያ ክስ ቀርቦበታል። ይህ ክስም በዕድሜ ልክ እሥራት ወይም በሞት የሚያስቀጣ ነው።

 

. ተከሳሽ ምን አለ?

ተከሳሹ ክሱን እቃወማለሁ አለ። የክስ መቃወሚያውም አስገድዶ መድፈር ወንጀሉን ለመደበቅ ከባድ ግድያ ፈፅሟል ተብሎ ቢከሰስም አስገድዶ መድፈሩ የግድያ ወንጀሉን ለማቋቋም ስላገለገለ ሊከሰስ የሚገባው በሁለቱ ተደራራቢ ወንጀል ሳይሆን በአንድ ተጠቃሎ በግድያ ወንጀል ክስ ብቻ ነው የሚል ነበር።

የዞኑ ከፍተኛ ፍ/ቤትም ተከሳሹ አስገድዶ መድፈሩንም ሆነ ከዚያ በኋላ ግድያውን የፈፀመው በሁለት የሀሳብ ክፍሎችና የሕግ ክፍሎች ስር ባሉ ድርጊቶች በመሆኑ በሁለት ተደራራቢ ወንጀሎች መከሰሱ ተገቢ ነው ብሎ መቃወሚያውን ውድቅ አደረገው። አቃቤ ህግ ያቀረባቸውን ተጨማሪ የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች ተከሳሹ ሊያያዙ አይገባም ብሎ ቢቃወምም ፍ/ቤቱ ለፍትሕ አሰጣጥ ይረዳሉ በሚል መቃወሚያውን ውድቅ አድርጎታል።

በወንጀል ሥነ-ሥርዓት ሕጉ መሰረት ተከሳሹ ክሱ ደርሶት ተነቦለት የተከሰሰበትን ድርጊት እንዲገነዘበው ተደርጓልና ድርጊቱን መፈፀሙን ተጠየቀ። “ድርጊቱን አልፈፀምኩም ጥፋተኛ አይደለሁም” ሲል መልስ ሰጠ።

የዞኑ ዐ/ሕግም ተከሳሽ ክሱን ቢክድም ድርጊቱን መፈፀሙን የሚያስረዱ ሦስት ምስክሮች ስላሉ ቀርበው ያስረዱልን ሲል ጠየቀ። ምስክሮቹም ቀርበው መሰከሩ።

 

1ኛ ምስክር የሔቨን አክስት ምን አለች?

በወቅቱ በስፍራው የነበረችው የሔቨን አክስት እንዲህ መሰከረች። በዕለቱ ሐምሌ 25 ቀን 2015 ዓ.ም ከጠዋቱ ሦስት ላይ እኔ፣ ሔቨን እና ትንሽ እህቷ እቤት ውስጥ ነበርን። ተከሳሹ ባጃጅ ነበረችው እሷን ስለሸጠ ብዙ ጊዜ እቤት ነው የሚውል። የተከሳሹ ልጅ እና ሟች ሔቨን ከግቢው ሲጫዉቱ ከቆዩ በኋላ የተከሳሹ ልጅ ከግቢ ወጥታ አያቶችዋ ጋር ስትሄድ ሔቨን ወደ ቤት ተመልሳ ከመጣች በኋላ እኔ እና የሔቨን ታናሽ እህት ምግብ እየበላን እያለ ሽንት ቤት ብላ ወጥታ ሄደች።

የተከሳሽ እና የኛ ቤት አንድ ግቢ ነው። ሟች ስትዘገይብኝ ስጣራ አቤት አትልም። ከዛ ትንሽ እህቷ ወጣች እና እየሮጠች መጥታ ሮዛ ሮዛ ስትለኝ ወጥቼ ስሄድ  ሻወር የምንወስድበት ቤት አለ ከዛ ወድቃ ምላሷ ወጥቶ...ነበረው። እየጮህኩ ይዣት ልወጣ ስል ተዘግቶ የማያውቀው የውጭው በር  በውስጥ ተሸጉጧል። እሷን መሬት ላይ አስቀምጬ በሩን ከፍቼ ወደ ውጭ ይዣት ወጣሁ። ተከሳሽ ሶፋው ላይ ተኝቶ ቴሌቪዥን ከፍቶ ተጋድሞ ነበር። ይዣት ወጥቼ ስጮህ ምን ሁነሽ ነው አላለኝም። ከግቢውም አልወጣም። ሰዎች ቡዳ ነው አሉ። ከግንባሯ በኩል የነበረው ሰውነቷ ግን ቀዝቅዟል።

ከዛ ወደ አሜን ሆስፒታል እንደወሰዷት ትገልፅ እና ህፃኗ በሞተች በነጋታው ከተከሳሽ ቤት ብረት ምጣድ ለቡና መቁያ ልታመጣ ስትሄድ ከቤት ውስጥ  በሩ አካባቢ ከቤት ጥራጊ ጋር የሔቨንን አንድ እግር ጫማ እንዳገኘች ትገልፃለች። እንዲሁም ህፃኗ ከዛ በፊት ምንም አይነት ሕመም እንደሌለባት ገልፃ በሩ ከውስጥ ብቻ እንጂ ውጭ ሆኖ እንደማይቆለፍ እና ግቢው ውስጥ ከተከሳሽ በቀር ማንም ሰው እንደማይኖር ገልፃለች።

 

2ኛ ምስክር የሔቨን እናት ምን አለች?

በዕለቱ ሔቨን ታማለች ነይ ተብላ ከባልደረባዋ ጋር ወደ ቤቷ መሄዷን ትገልፃለች። ቤት ስንደርስ ህፃኗም ሆነች ሌላ ሰው የለም። ተከሳሹ ሶፋ ላይ ተቀምጦ አገኘሁት ልጄ ምንድን ነው የሆነችው ስለው ምንም ነገር አይናገርም ደንግጦ ይመለከተኛል። ሌላ ዘመድ የለኝም ሰው የምታውቅ አንተ ነህ። ምን እንደሆነች አላውቅም እባክህ ንገረኝ ብለው ከወትሮው በተለየ ሁኔታ ሊያናግረኝ አልቻለም። ቤት ያከራየኝም እሱ...በቃ ዝም...በግቢው ውስጥም ሆነ ውጭ ምንም ሰው የለም። በሩ ላይ እንዳለው እባክህ ምን እንደሆነች እና የት እንደወሰዷት ንገረኝ ስለው ከውጭ ሁለት ህፃናት መጡ። ምንድን ነው የሆነች ብዬ ስጠይቃቸው ቡዳ በልቷት ወደ ቡዳ ቤት ወስደዋታል አሉኝ።

እባክህ ቤቱን ምታውቀው ከሆነ ውሰደኝ ስለው አሁንም ፈዞ ዝም አለ። ከዛ ባልደረባዬ እና ባለ ባጃጁ አንተ ምን አይነት ሰው ነህ ብለው ከባጃጅ አስገቡት። በዳር ተቀምጦ ባጃጁ መንገድ እንደጀመረ ወደ አሜን ሆስፒታል አምጥተዋታል ሲሉኝ መጮህ ጀመርኩ። ስደርስ ተሸፍናለች ህይወቷ አልፏል አሉኝ። ሳያት ሰውነቷ ነጥቷል፣ ልብሷ በውኃ ርሶ ገላዋ ታጥቧል። ሰው ሁሉ እያለቀሰ እሱ ዝም ብሎ ይንቀጠቀጣል አያለቅስም። እሱ ከቤት እህቶቹ እና ቤተሰቦቹ ..ሰው ሁሉ ሰምቶ አብሮ ከህፃኗ ጋር ሲሄድ እሱ ከቤት እያለ ዝም ማለቱ....ሁለት ዓመት አብረን ኖረን ዝም ማለቱ እሱ ስለደፈራት እና ስለገደላት ነው ብላለች።

ታናሽ እህቷ በሰጠችው ምስክርነት ላይ ከቤቱ አገኘሁት ያለችው የህፃኗ አንድ እግር ጫማ ሌላኛው እግር ጫማ ከአስክሬኑ ጋር መኖሩን፣ ጠዋት አድርጋው የነበረው ፓንቷም የለም ነበር። ከዛ ለተጨማሪ ምርመራ ወደ ህይወት ፋና ሆስፒታል ስንሄድ መርማሪ ፖሊሷ መረመረችው። ሌሎች እያለቀሱ እሱ ይንቀጠቀጣል ወዲህ ወዲያ ይላል። በአንፑላንሱ ጋቢና አስገብተው ወሰዱት ከዛ ቤት ከደረሰ በኋላ ሹልክ ብሎ ቤቱ ገብቶ ተቀመጠ። መደፈሯ ለማንም ሳይነገር እሱ ሆስፒታል መፀዳጃ ቤት ገብቶ በስልክ ተደፍራ ነው ይል ነበር። ከዛ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ተወሰደ።

 

3ኛ ምስክር የፎረንሲክ ሕክምና ስፔሻሊስትስ ምን አለ?

ሀኪሙ ፍ/ቤት ቀርቦ በሰጠው ቃል ሟች አስክሬን ላይ ባደረኩት ምርመራ ሰውነቷ ቀዝቅዟል፣ ከዓይኗ ቆብ በታች የታችኛው የዓይኗ ክፍል ገብቷል፣ ልብሷ በውኃ ረጥቦ ነበር።ከ አፏ ላይ ምን ያህል እንደሆነ ባላውቅም አፈር አለ ትንሽ ጠጠርም አለ ጠጠር የተቀላቀለበት፣ አንገቷ አካባቢ  በቀኝ በኩል ከፍ ብሎ ወደ አራት ሴንቲ ሜትር የሚሆን በፊት ለፊት አንገቷ ላይ የሚታይ የመንጣት ነገር አለ ከሌላው ሰውነቷ በተለየ ማለት ነው። በተጨማሪም ጭኗ በውጭኛው አካባቢ የተወሰነ መጋጋጥ ነበራት። ክብረ ንፅሕናዋን በተመለከተ የተወሰነ የመስፋት ነገር ይታይበት እንደነበር እና ዙሪያው የመቅላት ምልክት ይታይበት ነበር። ከማሕጸኗ በወሰድነው ናሙና የዘር ፍሬ አልተገኘበትም። ጀርባዋ እና እጆችዋ ላይም መጋጋጥ እንደነበረው ያሳያል ሲል ቃሉን ሰጥቷል።

ፍ/ቤቱም የዐ/ሕግ ምስክሮች እንደ ክሱ ስላስረዱ ተከሳሹ እንዲከላከል ብይን ሰጠ።

 

. የተከሳሽ ምስክሮችስ ምን አሉ?

ተከሳሽ አራት ምስክሮችን አቅርቧል። አራቱ ምስክሮች በሰጡት ቃልም በግቢው ውስጥ ጩኸት እንዳልነበረ፣ ሟችን የእናቷ እህት ከግቢ ይዛት ወጥታ እንዳዩ እና አሜን ክሊኒክ እንደወሰዷት፤ አንደኛዋ እምነት አፏ ላይ አድርጌላታለሁ አሜን ክሊኒክ ህይወቷ አልፏል መባሉ እና የሞተችበት ምክንያት ተደፍራ ነው ተብሎ እንደሰሙ፤ አንደኛዋ ደግሞ የወንቅሸት ሁለት ሌትር ፀበል ነበረኝ ፀበሉን ደፍቼባታለሁ። የሞተችው አንዴ ታንቃ ነው አንዴ ተደፍራ ነው ይሉናል በማለት መስክረዋል።

 

. የፍ/ቤቱ ውሳኔ

ሔቨን ተደፍራ አንገቷ ታንቆ ህይወቷ ማለፉን በቀረቡት ማስረጃዎች ማረጋገጡን ገልፆ፤ በወቅቱ ከተከሳሽ ውጭ በግቢው ውስጥ ሌላ ወንድ ያልነበረ እና የግቢው በርም ከወትሮው በተለየ ሁኔታ ከውስጥ በኩል መሸጎጡና ግቢው ዙሪያውን በአግባቡ የታጠረ በመሆኑ ሌላ ሰው ወደ ግቢው ገብቶ ወንጀሉን ፈፅሟል ሊባል የሚችል አይደለም። ተከሳሽ አከራይ ሆኖ እያለ ህፃኗ ወድቃ እንደተገኘች ሲጮህ ዝም ብሎ መቀመጡ እና እናቷም ልጅቷ የት እንዳለች ስትጠይቀው መልስ ሳይሰጥ ይንቀጠቀጥ የነበረ መሆኑ፣ አንድ እግር ጫማዋ ከቤቱ ከጥራጊ ጋር መገኘቱ እና በህፃኗ  ላይ አስገድዶ መድፈር መፈፀሙን ሆስፒታል ስትደርስ ህይወቷ አልፎ እደነበር አንገቷ ላይ የእጅ ጭረት ምልክት እንደነበር ሰውነቷ እና ልብሷ በውኃ ርሶ እንደነበር  ከፈለገ ህይወት ሆስፒታል እና ከአሜን የሕክምና ማዕከል በተፃፉ የሰነድ ማስረጃዎች መረጋገጡን ጠቅሷል።

ፍ/ቤቱም ህፃኗን ተከሳሹ እየደፈራት እያለ በወሰደው የኃይል እና የማነቅ ተግባር ገና ለጋ ህፃን ስለሆነች ጫናውን መቋቋም አቅቷት ህይወቷ ያለፈ መሆኑን ደምድሟል።

ተከሳሹ ሔቨንን ከደፈራት በኋላ ወንጀሉን ለመደበቅ ሲል ገደላት የሚለውን ሁለተኛውን ክስ ግን ማስረጃ አልቀረበበትም ሲል በወንጀል ሕግ 620(3) ስር ብቻ ጥፋተኛ ብሎታል።

 

. ስለ ቅጣቱ

ዐ/ሕግ ተከሳሽ ጥፋተኛ የተባለበት የወንጀል ድንጋጌ በቅጣት አፈፃፀም መመሪያው መሰረት ደረጃ እና እርከን ስለወጣለት በደረጃ አንድ በእርከን 38 ላይ አርፎ ቅጣት እንዲወሰንለት እና ተከሳሽ ድርጊቱን የፈፀመው እራሷን መከላከል የማትችል የ6 ዓመት ልጅ ላይ በመሆኑ እንደ ቅጣት ማክበጃ ይያዝልኝ ብሏል። ተከሳሽ ቅጣት ማክበጃውን ተቃውሞ የወንጀል ሪከርድ የሌለብኝ እና የቤተሰብ አስተዳዳሪ መሆኔ ከግምት ገብቶ ቅጣት ይወሰንልን ብሏል።   ፍ/ቤቱም ተከሳሽ በ25 ዓመት ፅኑ እሥራት እንዲቀጣ ወስኗል።

 

. ስለመረጃው ምንጭ

ይህን መረጃ የተገኘው በማኀበራዊ የትስስር ገጾች ላይ እየተዘዋወረ ከሚገኘው እና ወንጀሉን አስመልክቶ በመጽሔት ወጥቶ ከነበረ ጽሑፍ ነው፡፡ ጽሑፉ ከመፅሔቱ ገፅ ላይ አስተማሪ ውሳኔ በሚል ከገፅ 10-13 ላይ በፎቶ ተነስቶ የተሰራጨ ነው፡፡ ምስሉ ላይ ጥቂት ቦታዎች በብርሃን ነፀብራቅና በመደብዘዝ ምክንያት ያልታዩኝን ፊደላት ወይም ቃላት...ብዬ ከማለፌ በስተቀር ሙሉ ለሙሉ ነው ያቀረብኩት።ምናልባት ትክክለኛው ውሳኔ  ይሄ አይደለም የሚል አካል ካለ ማስረጃውን ማቅረብ የሚችል ሲሆን እዚህ ውሳኔ ላይ ከተጠቀሱት የሕግና የማስረጃ ጉዳዮች አንፃር ነው ለመገናኛ ብዙሃን ከተንሸራሸረው መረጃ በተጨማሪ ውሳኔውን ለማየት የሞከርኩት።

 

  1. የተከሳሽ መቃወሚያና የፍ/ቤቱ ውሳኔ

ተከሳሽ ልከሰስ አይገባም ሚለው በአስግድዶ መድፈሩ በመሆኑ በግድያው ወንጀል ብቻ ነው ልከሰስ ሚገባው ብሎ ክሱን ተቃውሟል። ፍ/ቤቱ ይህን መቃወሚያ ባይቀበለውም ተከሳሹ እንዲከሰስ የጠየቀበትን አስገድዶ መድፈሩን ለመደበቅ የተፈፀመ የግድያ ወንጀል ክስ ውድቅ አድርጎ በአስገድዶ መድፈር ወንጀል ብቻ ወስኖበታል። ይህ ፍ/ቤቱ በፍርዱ ላይ ሊተነትነው እና ሕጋዊ ምክንያቱን ሊያስቀምጥበት ይገባ የነበረ ቢሆንም ውሳኔው ላይ እንደታለፈ ያሳያል።

 

  1. ክሱ የቀረበበት አንቀፅ

ፍ/ቤቱ በውሳኔው ላይ እንደጠቀሰው ፌቨን ድርጊቱ ሲፈፀምባት ዕድሜዋ ሰባት ዓመት ነበር። በዚህ ዕድሜ ለሚገኙና ከ13 ዓመት በታች ላሉ ሕፃናት ደግሞ ሕጉ ልዩ ድንጋጌ አስቀምጧል።

በወ/ሕ/አ 627(5) መሰረት በዚህ የዕድሜ ክልል ካለች ህፃን ጋር የግብረ ሥጋ ግንንኙነት በመፈፀሙ ምክንያት ድርጊቱ ልጅቷ ላይ ሞት ካስከተለ ቅጣቱ የዕድሜ ልክ ጽኑ እሥራት ነው።

ዐ/ሕግ ክስ ያቀረበው ግን በማንኛውም ሴት ላይ ወይም ሕፃን ባልሆነች ሴት ላይ አስገድዶ መድፈር ወንጀል ሞት ሲያስከትል በሚያስጠይቀው አንቀፅ 620(3) መሰረት ነው። ስለዚህ ክሱ ሔቨን ባለችበት የህፃንነት ዕድሜ እና በድርጊቱ ምክንያት የተከሰተባትን ሞት ከግምት አስገብቶ ከ25 ዓመት በላይ የፅኑ እስር ቅጣት ወይም እድሜ ልክ የእሥር ቅጣት በሚያስቀጣው አንቀፅ ስር መቅረብ ነበረበት። ስለዚህ ክሱ ከአቀራረቡም ጀምሮ ክፍተት የታየበት ይመስላል።

 

  1. የፍ/ቤቱን የማስረጃ ምዘና እና ድምዳሜን በተመለከተ

በፍርዱ ላይ ከተጠቀሱት ማስረጃዎች ፍ/ቤቱ ሔቨን ተከሳሹ አስገድዶ እንደደፈራት አረጋግጧል። የሰነድ ማስረጃው ሚያሳየው አሜን የህክምና ማዕከል ስትደርስ ህይወቷ አልፎ እንደነበር አንገቷ ላይ የእጅ ጭረት ምልክቶች ነበሩ ነው። የስፔሻሊስት ሀኪሙም አንገቷ ላይ ከሌላው የሰውነቷ ክፍል በተለየ የመንጣት ምልክት እንደነበር አስረድቷል።

የተከሳሹ ምስክሮችም ፍ/ቤቱም እንደጠቀሰው ክሱን ሚያጠናክር እንጂ ሚያስተባብል ቃል አልሰጡም። ፍ/ቤቱ አስገድዶ ደፍሯት ድርጊቱን ለመደበቅ ገድሏታል የሚለውን ክስ ዐ/ሕግ አላስረዳም ያለው ከምን አግባብ ተነስቶ እንደሆነ ግልፅ አይደለም። ይሁንና ፍ/ቤቱ በውሳኔው ላይ ተከሳሽ እስገድዶ እየደፈራት በነበረበት ወቅት በወሰደው የኃይልና የማነቅ ተግባር ገና ለጋ ህፃን ስለሆነች ጫናውን መቋቋም አቅቷት ህይወቷ ማለፉን ከሁኔታዎች መደምደም ችለናል ብሏል።

የቀረቡት ማስረጃዎች ግን ተከሳሹ አስገድዶ በመድፈር ላይ እያለ ህይወቷ ማለፉን የሚያሳዩ ሳይሆኑ አስገድዶ ደፍሯት ወይም ሲደፍራት ወይም ከዛም በኋላ እንደሚገድላት አውቆና በወ/ሕ/አ 58(1)(ለ) መሰረት ውጤቱን ተቀብሎት ሻወር መውሰጃ በተባለው ሥፍራ እንደጣላትና ድርጊቱን የፈፀመው ቤቱ ውስጥ ሊሆን እንደሚችል ነው። ይህም የሚያሳየው በፍ/ቤቱ የድምዳሜ አቅጣጫ እንኳን ብንሄድ በወ/ሕ/አ 60(ለ) መርህ መሰረት በአንድ የአስገድዶ መድፈር ድርጊት አስገድዶ የመድፈርና ከባድ ግድያ በመፈፀም ጣምራ ወንጀሎችን መፈፀሙን ነው።

በመሆኑም የፍ/ቤቱ ድምዳሜ ህፃን ሔቨን በአንድ የወንጀል ድርጊት ሂደት ላይ መሞቷን የሚያሳይ ወይም የዐቃቤ ሕግ ምስክሮችን እና ክሱን አላስረዳም ያለበትን የሕግ አግባብ የሚያሳይ ነው ለማለት የሚያስደፍር አይደለም።

በርግጥ የወንጀል ጥፋተኝነት በማያጠራጥር ሁኔታ መረጋገጥ ቢኖርበትም አስገድዶ መድፈር እና ያን ለመሰወር የሚደረጉ ድርጊቶች በባህሪያቸው ሰው እያየ የሚፈፀሙ ባለመሆናቸው በአካባቢያዊ ማስረጃዎች ላይ የሚመሰረቱ ናቸው።

በመሆኑም ተከሳሹ ቤቱ ከልጁ ጋር ስትጫወት የነበረችውን ሔቨንን ደፍሮ  ሌላ ሰው ወንጀሉን እንደፈፀመባት  ለማስመሰል አንድ እግር ጫማዋ ከተገኘበት ከቤት ውጭ አውጥቶ መጣሉ እና ከዛም ዝም ብሎ ሲጠብቅ የነበረ መሆኑን በምስክሮች ቃል ያረጋገጠው ፍ/ቤቱ ሁለተኛውን የከባድ ግድያ ክስ ውድቅ ለማድረግ የሚያበቃው የሕግና የማስረጃ ድጋፍ መኖሩን አጠያያቂ ያደርገዋል።

 

. የቅጣቱን ተመጣጣኝነት በተመለከተ

በወንጀል ሕጋችን ላይ ወንጀሎች ተደራራቢ ሊባሉ የሚችሉባቸው እና የሚያስከትሉት ቅጣት ሊቀልና ሊከብድ ሚገባበት አግባብ ተቀምጧል።የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ያወጣው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ አለ። በዚህ መመሪያ መሰረት ውሳኔው ላይ ዐ/ሕግ የጠቀሰው ያልተሻሻለውን መመሪያ ቢሆንም አስራ ሦስት አመት ባልሞላት ልጅ ላይ የተፈፀመ የግብረ ሥጋ ወንጀል ሞት ካስከተለ ደረጃ አንድ እና እርከን 38  ላይ እንደሚወድቅ መመሪያ ቁ 2/2006 ይደነግጋል። ይህ እርከን ደግሞ ከዕድሜ ልክ እስራት እስከ ሞት ቅጣት የሚደርስ ነው። ተከሳሹ ጭካኔውን በሚያሳይ ነውረኝነት የሰባት አመቷን ህፃን ደፍሮ መግደሉና አስክሬኗን  ከቤቱ አውጥቶ መጣሉ  ጥፋቱን ለማክበድ በቂ በመሆናቸውን እና ቤተሰብ ማስተዳደሩ ወይም ወንጀል አለመፈፀሙ ብቻ ቅጣቱን ከማክበጃዎቹ በላይ ሊያቀሉለት ስለማይገባ ቢያንስ በእድሜ ልክ እስር ሊቀጣ ይገባው ነበር ብዬ አምናለሁ።

 

. ክሱ የቀረበበትን አንቀፅ በተመለከተ

ክሱ የቀረበበትን አንቀፅ በተመለከተ ፍ/ቤቱም ፌቨን የሰባት ዓመት ህፃን በመሆኗ ሕጉ በዚህ እድሜ ክልል ያሉ ህፃናትን ላይ የሚፈፀም አስገድዶ መድፈር ወንጀልን በሚመለከተው በአንቀፅ 627(5) ስር ተሻሽሎ እንዲቀርብ ማዘዝ ነበረበት። ዐ/ሕግ ክሱን በዚህ ድንጋጌ ስር ያላቀረበበትና ፍ/ቤቱም ቢያንስ  ለፍትሕ አሰጣጥ ሲል ይህን ያላዘዘበት ምክንያትም ግልፅ አይደለም።

 

. የሔቨን ዕድሜና ሁኔታ

ሕፃናት  ልዩ ጥበቃ ስለሚያሻቸው ውሳኔዎችም መወሰን ያለባቸው ለጥቅምና ለደህንነታቸው ቅድሚያ በሰጠ መልኩ ነው። በመሆኑም በሔቨን ላይ የቀረበው ክስም ሆነ የተሰጠው ውሳኔ ይህን ሕገ-መንግስታዊ መርህ ባገናዘበ መልኩ መሆን ይገባው ነበር። የ7 ዓመት እድሜ ያላት ልጅ በገዛ ግቢያቸው ውስጥ በተከሹ  አከራይነት በተከራዩት እና ከሁለት ዓመት በላይ አብራ የኖረችና ቤተሰቦቿም ለደህንነቷ አስተማማኝ ነው ብለው በሚያስቡት እና በምታስበው ግቢ  ውስጥ እያለች ነበር ድርጊቱ የተፈፀመው። ከተከሳሽ ልጅ ጋር ስትጫወት ቆይታ ሰው እንዳይደርስበት ግቢውን ከውስጥ ዘግቶ ድርጊቱ ፈፅሞባት 'ሻወር መውጃችን' የተባለው ስፍራ ላይ እንደጣላት  ከምስክሮች ቃል መረዳት ይቻላል። ድርጊቱን ለመሰወር የተደረጉ የማጠብ ድርጊቶች እንዳሉም እናትየው መስክራለች። ይህን የሚያስተባብል ማስረጃ ባልቀረበበት እምነት ሰጠናት ፀበል አፈሰስንባት ያሉ ምስክሮች ቃል መኖሩ ብቻ ተከሳሹ ድርጊቱን ሆን ብሎ ፈፅሞ ለመደበቅ የሄደባቸው ሂደቶች ላይ ጥርጣሬ ለማጫር የሚያበቁ ናቸው ብዬ አላምንም።

 

 

. ውሳኔው ለሔቨን ፍትሕ መስጠቱን እና አስተማሪነቱን በሚመለከት

ክሱ መቅረብም ሆነ መወሰን ያለበት የ7 ዓመቷ ሔቨን ላይ የተፈፀመውን አሳዛኝ ድርጊት የወንጀል ሕጉ በሚፈቅደው አግባብ ፍትሕ በመስጠት እና በዚህ ዕድሜ ያሉ ልጆች የሚያስፈልጋቸውን የሕግ ጥበቃ በሚያጠናክር መልኩ ሌሎችንም በሚያስተምር እና በሚያስጠነቅቅ አግባብ ከፍተኛውን የቅጣት ደረጃ ለመወሰን በሚያስችል መልኩ ነበር።

 

. ባሁኑ ጊዜስ የሔቨን ጉዳይ ምን ላይ ነው?

የዞኑ ዐ/ሕግ ስለ ክሱ አቀራረብ እና ውሳኔውን ተከትሎ ለይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት ይግባኝ ስለማቅረቡ ተገቢውን መረጃ ለሕዝብ ይፋ ማድረግ አለበት ብዬ አምናለሁ።

በድጋሚ ይህ ፅሑፍ የጸሐፊውን ግንዛቤ እና ይፋ ከተደረጉት መረጃዎች በተጨማሪ የፍ/ቤቱ ውሳኔ ነው ተብሎ በማኀበራዊ የትስስር ገጾች በተለቀቀ ጽሑፍ ላይ የተመሰረተ በመሆኑ ያን ታሳቢ ተደርጎ እንዲነበብ ጠይቃለሁ።

 

ማሳረጊያ መልዕቴም ፍትሕ ለሔቨን አወት። ሕጋዊውን ሥርዓት ተከትሎ ፍትሕን የሚያሰፍን እና መሰል ወንጀሎች ሕፃናት ላይ  እንዳይፈፀሙ የሚያስተምር እና የሚያስጠነቅቅ ውሳኔ ሊወሰን ይገባል የሚል ነው።

 

(የሕግ ባለሙያው ኪዳኔ መካሻ ለEBC Cyber የፃፈው)


ተያያዥ ርዕሶች

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top