የብላቴ የኮማንዶ እና አየር ወለድ ማሰልጠኛ ማዕከል በመሰረታዊ ኮማንዶና በፀረ ሽብር ልዩ ኃይል ለተከታታይ 6 ወራት ያሰለጠናቸውን ኮማንዶዎች የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በተገኙበት እያስመረቀ ነው።
የኢፌዴሪ የሀገር መከላከያ ሠራዊት ዘመኑ የሚጠይቀውን የሰለጠነ ወታደር ለማፍራት በትኩረት እየሰራ መሆኑን የገለፁት ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ፤ የኮማንዶና አየር ወለድ ዕዝ በልዩ ትኩረት እንዲደራጅ መደረጉን ተናግረዋል።
የኮማንዶ ኃይል የጦርነት ሁኔታን ቀያሪ የምድር ድሮን ነው ሲሉም ገልፀውታል።
የኮማንዶ አባላቱ በቀንና በሌሊት የሚሰጡ ፈታኝ የመሰረታዊ ኮማንዶ ስልጠናዎችን በብቃት ተወጥተው የተመረቁ መሆናቸውን የኮማንዶና አየር ወለድ ትምህርት ቤቱ ገልጿል።
አስቸጋሪውን ስልጠና በብቃት የተወጡት ሰልጣኞቹ ኢትዮጵያን ከየትኛውም የውጪም ሆነ የውስጥ ጠላት ለመመከት የሚያስችል የሰማይ፣ የምድር እንዲሁም የባህር ላይ የጦር ግዳጅን በብቃት ለመወጣት አስፈላጊውን ዝግጁነት የተላበሱ መሆናቸው ተገልጿል።
ተመራቂ ኮማንዶዎች የተለያዩ ትእይንቶችን ያቀረቡ ሲሆን፤ የጦርነት ሁኔታን ለመቀየር ያላቸውን ዝግጁነት በምርቃት ሥነስርዓቱ ላይ አሳይተዋል።
በተመስገን ሽፈራው