ኢትዮጵያ ያዘጋጀችው 37ኛው የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ በሁሉም ረገድ ስኬታማ ነበር

5 Mons Ago
ኢትዮጵያ ያዘጋጀችው 37ኛው የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ በሁሉም ረገድ ስኬታማ ነበር

ላለፉት ቀናት በአዲስ አበባ የተካሄደው 37ኛው የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ ዛሬ በስኬት ተጠናቋል።

ጉባዔው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ምክክር፣ የመሪዎች መደበኛ ጉባዔ እና የኅብረቱ ተቋማት ውይይቶች በስኬት የተከናወኑበት ነበር።

በተጨማሪም የሀገራት የጎንዮሽ ውይይቶችም በስኬት የተካሄዱበት ጉባዔ ሆኖ አልፏል።

ኢትዮጵያ ከጉባዔው ቅድመ ዝግጅት ጀምሮ እስከ ማጠናቀቂያው ድረስ በርካታ ስኬቶችን አስመዝግባለች።

ኢትዮጵያ የአፍሪካን አጀንዳዎች ከፍ ከማድረግ በተጨማሪ የራሷን አጀንዳዎች እና የሁለትዮሽ ውይይቶችን በተሳካ ሁኔታ አከናውናለች።

የጉባዔው መስተንግዶም አንዱ የኢትዮጵያ ስኬት ነበር። ለጉባዔው የተቀናጀ ቅድመ ዝግጅት በመደረጉ ለጉባዔው የመጡ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች፣ የዓለም አቀፍ ተቋማት ተወካዮች እና ሌሎች ተሳታፊዎችን ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲያዊ ክብርን በጠበቀ መልኩ ተቀብላ እና አስተናግዳ መሸኘት ችላለች።

በመስተንግዶው የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች ከፀጥታ አካላት ጋር በመተባበር እንግዶቹ ኢትዮጵያ እንደ ሁለተኛ ቤታቸው እንድትሰማቸው አድርገዋል።

ጉባዔው ከተጀመረ በኋላም የአፍሪካ አጀንዳ ዓለም አቀፍ አጀንዳ እንዲሆን በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሚዲያዎች ሽፋን እንዲሰጥ ተደርጓል። 

በሌላ በኩል በጉባዔው ኢትዮጵያ የራሷን ዋና ዋና አጀንዳዎች አሳክታበታለች። በዚህም ትምህርትን ጨምሮ ዋና ዋና ሀገራዊ ስኬትችን ማንጸባረቅ የቻለችበትም ነበር።

ጉባዔው የጥቁር ሕዝቦች ማማ ከሆነው የዓድዋ ድል መታሰቢያ ምርቃት ጋር መተሳሰሩ እና የጉባዔው ተሳታፊዎች በመታሰቢያው ያደረጉት ጉብኝትም ለጉባዔው ልዩ ድባብ ፈጥሯል።

ኢትዮጵያ ከጉባዔው ጎን ለጎን ራሷ በቀረጸቻቸው አጀንዳዎች ላይ ያዘጋጀቻቸውን መድረኮችም በስኬት አከናውናለች።

ሀገሪቱ ከጉባዔው ጎን ለጎን ብሔራዊ ጥቅሞቿን ሊያሳኩ የሚችሉ በርካታ የሁለትዮሽ ስምምነቶችን ከተለያዩ ሀገራት እና ተቋማት ጋር ማከናወን የቻለችበት ሆኖ አልፏል።

በለሚ ታደሰ


ተያያዥ ርዕሶች

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top