ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዘላቂ የክትመት ሽግግርን ለማሳካት ቁርጠኛ ናት፡- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ

12 Days Ago 164
ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዘላቂ የክትመት ሽግግርን ለማሳካት ቁርጠኛ ናት፡- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዘላቂ የክትመት ሽግግርን ለማሳካት ቁርጠኛ ናት ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ተናገሩ።
 
የመጀመሪያው የአፍሪካ ከተሞች ፎረም "ዘላቂ የከተሞች ልማት ለአፍሪካ ትራንስፎርሜሽን አጀንዳ 2063" በሚል መሪ ሀሳብ ከዛሬ ጀምሮ ለሦስት ቀናት በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል።
 
በፎረሙ መክፈቻ ንግግር ያደረጉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፥ ኢትዮጵያ የፓን አፍሪካን እሳቤዎች እውን ለማድረግ ለረጅም ዘመን የተግባር ቁርጠኝነቷን አሳይታለች ብለዋል።
 
የነገ የአፍሪካ ክትመትን የተሻለ ለማድረግ የሚመክረውን ጉባኤ በማስተናገዷ ክብር እንደሚሰማት ጠቅሰው፤ የአፍሪካ ከተሞች ፎረም የአህጉራችንን ልማት ወደፊት ለማራመድ የጋራ ቁርጠኝነትን የምናሳይበት ነው ብለዋል።
 
ፎረሙ ስለ አፍሪካ ዕድገት ሀሳቦችን ለመለዋወጥ፣ ዘላቂ፣ አካታችና የበለጸጉ ከተሞች እንዲኖሩ በጋራ ለመሥራት ግብ የሚቀመጥበት ወሳኝ መድረክ መሆኑን ጠቁመዋል።
 
በአጀንዳ 2063 የምንመኛትን የአፍሪካ ክትመት የመፍጠር ራዕይን ለማሳካትና ለችግሮች አህጉራዊ መፍትሔ ለመስጠት እንደሚያስችልም አንስተዋል።
 
አሁን እያጋጠሙ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት ከተለመደው አካሄድ መውጣት እንደሚገባ ጠቅሰው፤ ከአህጉራዊ ግቦች አንፃር ተለዋዋጭ የፖለቲካ ስልትና ጠንካራ ውሳኔ ማሳለፍ ይገባል ብለዋል።
 
ኢትዮጵያ አኩሪ ታሪክና ዕድሜ ጠገብ የዲፕሎማሲ ልምድ ያላት ከመሆኗ አኳያ የጋራ አህጉራዊ ምኞቶን በማሳካት ረገድ በፅናትና በቁርጠኝነት ስትሰራ መቆየቷን አንስተው፤ አሁንም የመሪነት ሚናዋን ታጠናክራለች ብለዋል።
 
አፍሪካ የከተማ ትራንስፎርሜሽን ላይ ትገኛለች ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ ከተሞቿ በፍጥነት እያደጉ መሆናቸው ዕድልም ፈተናም ይዞ መምጣቱን ጠቁመዋል።
 
ከተሞች ውጤታማ በሆነ መንገድ ከተመሩ ትልቅ የልማት አቅም፣ የፈጠራ፣ የኢንዱስትሪና የሥራ ዕድል ፈጠራ ማዕከላት እንደሚሆኑም ጠቁመዋል።
 
ይሁን እንጂ ዛሬ ላይ በቂ ያልሆነ መሠረተ ልማት፣ የመኖሪያ ቤት እጥረት፣ ሥራ አጥነትና የአካባቢ ብክለትን ጨምሮ ከተሞች በርካታ ችግሮችን እያስተናገዱ መሆኑን አንስተዋል።
 
እነዚህ ተግዳሮቶች ውስብስብ በመሆናቸው አዲስ ዕይታን፣ አካታችና ፈጠራን የሚያበረታቱ ስትራቴጂካዊ እርምጃዎችን በመውሰድ ተፅዕኖን የሚቋቋም ዘላቂ ክትመትን መገንባት አለብን ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።
 
ከዚህ አኳያ የአፍሪካ ከተሞች ፎረም የአፍሪካን የወደፊት ዕጣ ፈንታ የሚቀርፁ የከተማ አጀንዳዎችን ለማንሳትና ለመተግበር ወሳኝ እድል እንደሚሰጥ ጠቁመዋል።

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top