የኢትዮጵያ አቪየሽን አካዳሚ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ 8 ስትራቴጂክ የቢዝነስ ዩኒቶች አንዱ ነው፡፡ ዩኒቨርስቲው በየዓመቱ 4 ሺህ ሠልጣኞችን የመቀበል አቅም ያላቸው አምስት ትምህርት ቤቶች አሉት።
የኢትዮጵያ አቪዬሽን ዩኒቨርስቲ በኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን ዕውቅና የተሰጠው የሥልጠና ተቋም ነው፡፡ የዓለም አቀፉ የሲቪል አቪየሽን ድርጅት (ICAO) የቀጣናው የሥልጠና ማዕከልነትን ዕውቅና አግኝቷል፡፡
በአውሮፓ አቪዬሽን ደህንነት ኤጀንሲ (EASA) በክፍል 147 የB737 እና B757/767 የጥገና ማሠልጠኛ ተቋምነት ማረጋገጫ አለው፡፡ በዓለም አቀፉ የአየር ትራንስፖርት ማኅበር (IATA) ማረጋገጫም ተሰጥቶታል፡፡ ሌሎች የዘርፉ ባለድርሻዎችም ለአካዳሚው የማረጋገጫ የምስክር ወረቀቶችን እና ሽልማቶችን አበርክተዋል፡፡
ዓለም አቀፉ የአየር ትራንስፖርት ማኅበር (IATA) የቀጣናዊ የሥልጠና አጋርም ነው የኢትዮጵያ አቪየሽን ዩኒቨርስቲ፡፡ በዓለም አቀፍ የአቪየሽን ማሰልጠኛ ተቋማት በተደረገ ምዘናም አራተኛውን ከፍተኛ ደረጃ ያገኘ ተቋም ነው፡፡
ከስድስት አስርት ዓመታት በላይ እድሜ ያለው የኢትዮጵያ አቪየሽን አካዳሚ በቀጣናው ትልቁ እና ዘመናዊ የበረራ እና ቴክኒክ ማሰልጠኛ ማዕከል ሲሆን፣ ምርጥ እና ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን የታጠቀ ነው።
የምስለ በረራ (simulator) ቴክኖሎጂ ፕሮግራምን በማስተዋወቅ እና በተሳካ ሁኔታ በማካሄድ ላይ ከሚገኙ ጥቂት የአፍሪካ የአቪየሺን የሥልጠና ማዕከላትም የመጀመሪያው ነው።
በአፍሪካ ደረጃ በፍጥነት በማደግ ላይ ያለው እና ትልቁ የአቪየሽን ሥልጠና አካዳሚ ተግባራዊ እና የሥራ ላይ ሥልጠናዎችን ለመስጠት የሚያስችሉ ዘመናዊ አውሮፕላኖች፣ የማሠልጠኛ መሣሪያዎች እና የጥገና ተቋማት ባለቤት ነው።