የሰሜን አፍሪካ ሀገሮች አዲስ ቀጣናዊ ቡድን ሊመሠርቱ መሆኑ ተገለፀ

11 Days Ago
የሰሜን አፍሪካ ሀገሮች አዲስ ቀጣናዊ ቡድን ሊመሠርቱ መሆኑ ተገለፀ
ቱኒዚያ፣ አልጀሪያ እና ሊቢያ ከቀድሞ የዓረብ ማግሬብ ህብረት (AMU) መስራቾች ሞሮኮ እና ሞሪታኒያ ውጪ አዲስ ቀጣናዊ ቡድን ሊመሰርቱ መሆኑ ተገልጿል።
 
የሶስቱ ሀገራት መሪዎች በአንዳንድ አባል ሀገራት መካከል በሚፈጠር ዲፕሎማሲያዊ ውጥረት ምክንያት ከአሥር ዓመታት በላይ የተቀዛቀዘውን የዓረብ ማግሬብ ህብረት እንደገና እንዲያንሰራራ በማሰብ የምክክር ስብሰባ መጀመራቸው ተነግሯል።
 
የቱኒዚያው ፕሬዚዳንት ካይስ ሳይድ ከአልጄሪያ አቻቸው አብደልማጂድ ቴብቡኔ እና የሊብያ ፕሬዚዳንታዊ ምክር ቤት መሪ መሐመድ ዩነስ ሜንፊ ጋር በመሆን የመጀመሪያውን “የሶስቱ እህት ሀገሮች” ጉባኤ ለማካሄድ ወደ ቱኒዚያ እንደሚመጡ በቀድሞው ትዊተር በአሁኑ ኤክስ ገፃቸው ላይ በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል።
 
የመጀመሪያው ስብሰባ የሚካሄድበት ቀን ባይገልጽም፤ ስብሰባው በቱኒዚያ ዋና ከተማ ቱኒስ እንደሚካሄድ የአካባቢው መገናኛ ብዙኀን መዘገባቸው ታውቋል።
 
አዲሱ ጥምረትም የአረብ ማግሬብ ህብረት ፖለቲካዊ እና ኢኮኖሚያዊ ቡድን አባላት የሆኑትን ሞሮኮ እና ሞሪታንያን በማግለሉም ትችት ተሰንዝሮበታል።
 
ይህ ጥምረት አልጀርስ በክልሉ ላይ እያሳደረች ያለውን ተፅዕኖ የሚያሳይ እንደሆነ እና ያለራባት አዲስ የቀጣናዊ ጥምረት ለመመስረት ሙከራ አድርጋለች በማለት ሞሮኮ መክሰሷም ተዘግቧል።
 
የአልጄሪያው ፕሬዚዳንት ቴብቡንም በበኩላቸው፤ጥምረቱ በየትኛውም ሌላ ሀገር ላይ ያነጣጠረ ምንም አላማ እንደሌለው እና ጥምረቱን መቀላቀል ለሚፈልጉ በአካባቢው ላሉ ሃገራት በሩ ክፍት ነው በማለት ከአልግ 24 ኒውስ ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ ክሱን ውድቅ ማድረጋቸውን አር ቲ ዘግቧል።

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top