የጆርዳን የቱሪዝም፣ የሀይማኖት እና የትምህርት ሴሚናር በሀገሪቱ ኤምባሲ አዘጋጅነት ተካሂዷል፡፡
በመርሀግብሩ ላይ ንግግር ያደረጉት የቱሪዝም ሚኒስትር አምባሳደር ናሲሴ ጫሊ፤ ታሪካዊ የሁለትዮሽ ግንኙነት ያላቸው ኢትዮጵያና ጆርዳን በቱሪዝም ዘርፍ ትብብራቸውን ለማጠናከር እንደሚሰራ ገልፀዋል።
በቱሪዝም ኢንቨስትመንት፣ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማስተዋወቅና፣ የቱሪዝም ጥቅሎችን በማዘጋጀት እና በአቅም ግንባታ ላይ በጋራ ለመስራት ከጆርዳን ቱሪዝም ሚኒስትር ጋር ስምምነት ላይ መደረሱን አንስተዋል::
የጆርዳን የቱሪዝም ሚኒስትር መክራም ሙስጠፋ በበኩላቸው፤ ጆርዳንና ኢትዮጵያ ለበርካታ ዓመታት የዘለቀ ጠንካራ ወዳጅነት ያላቸው አገራት መሆናቸውን ተናግረዋል።
ይህንን አጋርነት ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ የቱሪዝም ዘርፍ አንዱ መሆኑን ገልጸው፤ በዘርፉ በተለያዩ መስኮች ትብብርን ለማጠናከርና በጋራ ለመሥራት አገራቸው ቁርጠኛ መሆኗን መግለፃቸውን ከቱሪዝም ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።