ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ በኒውዮርክ ባሰሙት ንግግር ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም በአረንጓዴ ዐሻራ መርሐግብሯ አማካይነት አመርቂ ስራ በማከናወን ላይ መሆኗን ገልፀዋል።
ላለፉት 5 ዓመታት በተከናወነው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐግብር ከ32 ቢሊዮን በላይ ችግኞች መተከላቸውን ጠቅሰዋል።
ሀገሪቱ እንደየአደጋው ስፋት፣ ጥልቀት እና ድግግሞሽ ተለዋዋጭ የሆነ የአደጋ ቅድመ ማስጠንቀቅ ስርዓት እንደምትከተልም አብራርተዋል።
በተመድ ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ የተጀመረውን እና "የአደጋ ቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት ለሁሉም" የተሰኘውን ኢኒሼቲቭ ያደነቁት አቶ ደመቀ፤ ለተግባራዊነቱ የተቀናጀ ትብብር እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል።
በሀገር አቀፍ፣ በአህጉር አቀፍ እና በዓለም አቀፍ ደረጃ ብቁ እና ውጤታማ የሆነ የአደጋ ቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት ለመዘርጋት የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የገንዘብ ድጋፍም ወሳኝ መሆኑንም መናገራቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።