የሚኒስትሮች ምክር ቤት በ42ኛ መደበኛ ስብስባው በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳለፈ

5 Days Ago 141
የሚኒስትሮች ምክር ቤት በ42ኛ መደበኛ ስብስባው በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳለፈ

የሚኒስትሮች ምክር ቤት በዛሬው ዕለት ባካሄደው 42ኛ መደበኛ ስብሰባ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

በዚህም መሰረት፡-

  1. በቅድሚያ ምክር ቤቱ የተወያየው የኢትዮጵያ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ረቂቅ አዋጅ ላይ ነው፡፡ አዋጁ በተቋሙ የተጀመረውን የሪፎርም ስርዓት ወደ ተግባር በመለወጥ በኢትዮጵያ የህዝቡን የእርስ በእርስ መረዳዳት ባህል የማጎልበትና ተረጂነትን በዘላቂነት በሀገር አቅም መወጣትን ማዕከል በማድረግ የአደጋ ጉዳት ሰለባ ለሆኑ ዜጎች ከሰብአዊ ድጋፍ መርሆዎች፣ ከዘላቂ የልማት ፕሮግራሞችና ከሰላም መስፈን ጋር በማስተሳሰር ማህበራዊ፤ ኢኮኖሚያዊና ሞራላዊ ጉዳቱን ለመቀነስ የሚያስችል ነው፡፡ ምክር ቤቱም በጉዳዩ ላይ በሰፊው ከተወያየበት በኋላ ግብአቶችን በማከል ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡
  2. በመቀጠል ምክር ቤቱ የተወያየው በሦስት የተቋማት ማቋቋሚያ ረቂቅ ደንቦች ላይ ነው፡፡ የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ማቋቋሚያ ደንብ ዩኒቨርሲቲው አላማውን ለማሳካት የአደረጃጀት ማስተካከያዎችንና የአሠራር ለውጦችን ለማድረግ፤ የመከላከያ ስፔሻላይዝድ ሪፈራል ሆስፒታል ግሩፕ እና የመከላከያ ዲያግኖስቲክ ማዕከል ማቋቋሚያ ደንብ ተቋሙ የሀገሪቱን የልዕለ ህክምና፣ የዲያግኖስቲክ እና ተዛማጅ አገልግሎት ፍላጎትን ለማሟላት፤ እንዲሁም የተሻለ ህክምና ፍለጋ ወደ ውጭ ሀገር የሚሄዱ ታካሚዎች በሀገር ውስጥ አገልግሎቱን እንዲያገኙ ለማድረግ እንዲሁም የመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ግሩፕ ማቋቋሚያ ደንብ የተቋሙን ተግባርና ሀላፊነት በመደንገግ ለሀገር እድገት የበኩሉን ሚና እንዲወጣ ለማድረግ የህግ ማዕቀፍ ሆኖ የሚያለግ ቀርቧል።

ምክር ቤቱም በቀረቡት ረቂቅ ደንቦች ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ ግብዓቶችን በማከል በነጋሪት ጋዜጣ ታትመው ከወጡበት ቀን ጀምሮ በስራ ላይ እንዲውሉ በሙሉ ድምጽ መወሰኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ፅ/ቤት መረጃ ያመለክታል፡፡


አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top