ቻይና በደኅንነት ጉዳዮች ላይ ለመነጋገር ወደ ሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯን ላከች

10 Mons Ago
ቻይና በደኅንነት ጉዳዮች ላይ ለመነጋገር ወደ ሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯን ላከች

የዲፕሎማቱ ጉዞ ፕሬዚደንት ፑቲን በቅርቡ ለሚያደርጉት ታሪካዊው የቤይጂንግ ጉብኝት መሠረት እንደሚጥል ተዘግቧል።

ሞስኮ በዩክሬን እያካሄደችው ባለው ጦርነት ቀጣይነት ያለው ድጋፍ እየፈለገች ባለበት ወቅት የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ይ በጸጥታ ጉዳዮች ላይ ለመነጋገር ሩሲያ ገብተዋል።

የሞስኮ የቅርብ ወዳጅ የሆነችው ቤይጂንግ በዩክሬን ጦርነት ሩሲያን በተዘዋዋሪ ረድታለች በሚል ትከሰሳለች፤ ይሁን እንጂ ቤይጂንግ ክሱን በተደጋጋሚ ውድቅ አድርገዋለች።

የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዋንግ ይ ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት ወደ ሩሲያ ያቀኑት ቭላድሚር ፑቲን ከሰሜን ኮሪያው መሪ ኪም ጆንግ ኡን ጋር ተገናኝተው የጦር መሣሪያ ስምምነት እንዳደረጉ ከተነገረ በኋላ ነው።

የሩሲያ መገናኛ ብዙኃን የዲፕሎማቱ ጉዞ ፕሬዚደንት ፑቲን በቅርቡ ለሚያደርጉት ታሪካዊው የቤይጂንግ ጉብኝት መሠረት እንደሚጥል ዘግበዋል።

ለመጨረሻ ጊዜ ከአገራቸው ውጭ የተጓዙት እንደ አውሮፓውያኑ ታኅሳስ 2022 ሲሆን የሄዱትም ወደ ቤላሩስ እና ኪርጊስታን እንደነበር ቢቢሲ ዘግቧል።

የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እንዳለው፣ ዋንግ በሩሲያ ለአራት ቀናት የሚቆዩ ሲሆን በደኅንነት ጉዳዮች ላይ ይነጋገራሉ።

የሩሲያ የዜና ወኪል ታስም፣ መልዕክተኛው ከሩሲያው አቻቸው ሰርጌይ ላቭሮቭ ጋር እንደሚገናኙ ገልጾ፣ ዋነኛ መነጋገሪያቸውም የዩክሬን ጦርነት እንደሚሆን ክሬምሊንን ጠቅሶ ዘግቧል።

 


አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top