የፓን አፍሪካኒዝም ምልክት እና የአፍሪካ ቀዳሚ የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ የተለያዩ ሀገራት አየር መንገዶችን ድርሻ በመያዝ በአህጉሪቱ ቀዳሚነቱን እያሰፋ ይገኛል።
የፓን አፍሪካን ኔትዎርክ መፍጠር እና ማጠናከር ዓላማው የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አፍሪካን በአራቱም ማዕዘናት በማስተሳሰር የአፍሪካውያንን እርስ በርስ ግንኙነትን ለማጠናከር እየሠራ ይገኛል።
አየር መንገዱ በቪዥን የ2025 ስትራቴጂው አፍሪካን የማስተሳሰር በአፍሪካ ያለውን የገበያ ድርሻ ለማሳደግ ከያዛቸው ዕቅዶች መካከል አንዱ ከአህጉሪቱ አየር መንገዶች ጋር በትብብር መሥራት ነው፡፡ ይህም ስትራቴጂያዊ ሽርክና፣ የጋራ ባለቤትነት እና የአስተዳደር ስምምነቶችን መፍጠርን ይጨምራል።
በዚህም መሰረት በርካታ የአህጉሪቱ አየር መንገዶች የኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለው የዳበረ ልምድ እንዲያደራጃቸው እና ድርሻውንም እንዲይዝ ፍላጎታቸውን ማሳየት ከጀመሩ ቆይተዋል፡፡ አየር መንገዱም የተመረጡ አየር መንገዶችን ከ40 እስከ 49 በመቶ ድርሻ ይዞ መልሶ የማደራጀት ሥራውን ቀጥሏል፡፡
አየር መንገዱ በዚህ መንገድ ካደራጃቸው አየር መንገዶች መካከል "ኤርስካይ" የተሰኘው የቶጎ አየር መንገድ አንዱ ነው፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የኤርስካይ አየር መንገድን 40 በመቶ ድርሻ ይዞ እንደገና ያደራጀው እ.አ.አ በ2010 ነው፡፡ መነሻውን ሎሜ ቶጎ ያደረገው ‘ኤርስካይ’ በምዕራብ አፍሪካ ያሉ ሀገራትን ለማስተሳሰር ይሠራል፡፡ በዚህ መነሻም ከሀገር ውስጥ በረራ በተጨማሪ ከ20 በላይ ወደሚሆኑ የምዕራብ እና መካከለኛ አፍሪካ ሀገራት በረራውን ያደርጋል፡፡
የማላዊ አየር መንገድ ሌላው በኢትዮጵያ አየር መንገድ 49 በመቶ ድርሻ እ.አ.አ በ2013 መልሶ የተደራጀ አየር መንገድ ነው፡፡ ቀድሞ የነበረው የማላዊ አየር መንገድ ከአገልግሎት ውጭ ከሆነ በኋላ ነው በማላዊ መንግሥት ጥያቄ አየር መንገዱ እንደገና የተመሰረተው፡፡ የማላዊ መንግሥት 51 በመቶ ድርሻውን የያዘ ሲሆን የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአስተዳደር፣ የአቅም ግንባታ እና ሌሎች ቴክኒካዊ ሥራዎችን በኃላፊነት ይሠራል፡፡
የዛምቢያ አየር መንገድ 45 በመቶ በኢትዮጵያ አየር መንገድ የተያዘ ሲሆን፣ ቀሪውን 55 በመቶ በባለቤትነት የያዘው የዛምቢያ መንግሥት ነው፡፡ ቀድሞ የነበረው የሀገሪቱ አየር መንገድ አገልግሎት ካቆመ በኋላ በኢትዮጵያ አየር መንገድ እ.አ.አ ዲሴምበር 2021 እንደገና የተደራጀው የዛምቢያ አየር መንገድ ቀጣናውን እያስተሳሰር እንደሚገኝ ይገለፃል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ እ.አ.አ በ2018 ከቻድ መንግሥት ጋር በመተባበር ቻድ አየር መንገድን ያቋቋመ ሲሆን፣ 49 በመቶ ባለበትነቱንም ይዟል።
49 በመቶ የናይጄሪያ አየር መንገድ ድርሻን ይዞ የአመራር እና ቴክኒካዊ ድጋፉን እንዲያደርግ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ተመርጧል። ይህም ኢትዮጵያ ምዕራብ አፍሪካ ያላትን ስትራተጂካዊ አጋርነት የሚያሳድግ እና የአየር መንገዱን ተፅዕኖም የሚያሰፋ ነው።
ሙሉ በሙሉ በኢትዮጵያ አየር መንገድ የተያዘው የሞዛምቢክ አየር መንገድ ባለቤትነት "የኢትዮጵያ ሞዛምቢክ አየር መንገድ" በሚል ተሰይሟል። ይህም አየር መንገዱ በደቡባዊ አፍሪካ ያለውን ገበያ በማስፋፋት ሁለገብ ተደራሽነቱን እውን እንዲያደርግ የሚያስችለው ነው፡፡
አየር መንገዱ በአቪዬሽን ዘርፍ ያዳበረውን ልምድ ለሌሎች የአፍሪካ አየር መንገዶችም እያካፈለ ሲሆን፤ በዚህም የአሠራር፣ የቴክኒክ እና የአስተዳደር ድጋፍ እያደረገ ይገኛል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሚሰጠው ምቹ እና ቀልጣፋ አገልግሎት ገቢውን እየሳደገ ሲሆን፤ በአፍሪካ እና ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለውን ተደራሽነቱን በማሻሻል የገበያ ተፎካካሪነቱን ወደ ላቀ ደረጃ አሳድጎታል፡፡
አየር መንገዱ የአህጉሪቱን የተለያዩ አየር መንገዶች በባለድርሻነት መያዙ በአፍሪካ አቪዬሽን ዘርፍ መሪ ስለመሆኑ አመላካች ሲሆን፣ ይህም የቀጣናዊ እና ዓለም አቀፋዊ ተደራሽነቱን በእጅጉ ያሰፋዋል።
እነዚህ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ኢንቨስትመንቶች አዲስ አበባ አውነተኛ የአፍሪካ እና የዓለም ማዕከል እንድትሆንም የሚያደርግ ነው፡፡
ትርፋማነት ከማሳደግ ባለፈም በአህጉሪቱ ውስጥ ያለውን የእርስ በርስ ግንኙነት በማጎልበት ቀጣናዊ እና አህጉራዊ የኢኮኖሚ ውህደትን አውን እንዲሆን የሚያስችል ነው፡፡
በለሚ ታደሰ