ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የ 10 ኪ.ሜ ሩጫ በዓለም አትሌቲክስ የውድድር ደረጃዎች ውስጥ ተካተተ

7 Days Ago 173
ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የ 10 ኪ.ሜ ሩጫ በዓለም አትሌቲክስ የውድድር ደረጃዎች ውስጥ ተካተተ

የዓለም አትሌቲክስ አስተዳዳሪ ዎርልድ አትሌቲክስ የ2017 ሶፊ ማልት ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ 10 ኪ.ሜ ሩጫን የሌብል ደረጃ ያለው የጎዳና ላይ ውድድር ሲል ዕውቅና ሰጥቶታል።

የአለም አትሌቲክስ የሌብል ደረጃ ሲል የሰየማቸው ውድድሮች በጥራት ዝግጅቶችን ከማድረግ፣ ደህንነታቸው የተጠበቀ ከመሆን እና የተሳታፊዎች ውድድሩ ላይ የነበራቸው ቆይታ፣ የከተማ አስተዳደሮች ለዝግጅቱ ያላቸውን ድጋፍ፣ እንዲሁም ዝግጅቱ በአትሌቲክስ ውድድር ዘርፍ አበረታች መድኃኒት ላይ ለመስራት ያለውን ቁርጠኝነት ከግምት ውስጥ ያስገባ መሆኑ ተጠቅሷል።

እጅግ በርካታ የሩጫ ውድድሮች ባሉበት ዓለም ይህንን የሌብል ደረጃ ማግኘት ዝግጅቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ ያሳየውን ዕድገት እና በዓለማችን ካሉ ቀዳሚ እና ተመራጭ የጎዳና ላይ ውድድሮች መሀከል መሆኑንም እንደሚያሳይ ተጠቁሟል።

የአለም አትሌቲክስ አስተዳዳሪው አካል (World Athletics) ውድድሮችን በመመዘን በየአመቱ ደረጃዎችን የሚሰጥ ሲሆን፤ የመሮጫ ኮርስ ልኬት፣ የውድድር ሰዓት ምዝገባ እና የኤሊት አትሌቶች ተሳትፎ ከግምት ውስጥ የሚገቡ ጉዳዮች ናቸው ተብሏል።

24ኛው ዙር ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ አለም አቀፍ 10ኪሜ ህዳር 8 ቀን 2017 በ50ሺ ተሳታፊዎች እንደሚካሄድ ከታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡


አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top