የአፋር ክልል ሀብት የሆነውን ጨው በፍትሀዊ መንገድ ለመጠቀም የሚያስችል ዘመናዊ አሰራር ተግባራዊ እንደሚደረግ ተገለፀ

13 Days Ago
የአፋር ክልል ሀብት የሆነውን ጨው በፍትሀዊ መንገድ ለመጠቀም የሚያስችል ዘመናዊ አሰራር ተግባራዊ እንደሚደረግ ተገለፀ

የአፋር ክልል ሀብት የሆነውን ጨው በፍትሀዊ መንገድ የክልሉ ህብረተሰብ ተጠቃሚ ሆኖ ሌላውም እንዲጠቀምበት የሚያስችል ዘመናዊ አሰራር ተግባራዊ እንደሚደረግ ተገልጿል፡፡

በንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ፍስሃ ይታገሱ የተመራ ልኡክ በአፋር ክልል የንግድ ስርዓቱን ለማሳለጥ እየተከናወኑ ባሉ ስራዎች ዙሪያ ከክልሉ ርዕሰ መስተዳደር አቶ አወል አርባ ጋር ተወያይቷል፡፡

በውይይቱ ወቅት፤ ክልሉ በተለያዩ መስኮች ሰፊ አቅም ያለዉ መሆኑን ያነሱት አቶ ፍስሃ ይታገሱ፤ ለዚህም ባለፋት 5 አመታት ክልሉ ያከናወናቸዉ ተግባራት አበረታችና ተስፋ ሰጪ መሆናቸዉን ተናግረዋል፡፡

ሚኒስትር ዴኤታዉ አክለውም፤ ጨዉን ጨምሮ በማዕድን ዘርፉ ክልሉንም ሆነ ሃገሪቷን ይበልጥ ተጠቃሚ ለማድረግ የገበያ ትስስሩን በማቀላጠፍ ረገድ ሚኒስቴሩ በርካታ ስራዎች በማከናወን ላይ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡

የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳደር አቶ አወል አርባ በበኩላቸው፤ ክልሉ በማዕድን፣ በእንስሳት፣ በቱሪዝም መስህቦች እና በእንስሳት ሃብት የታደለ መሆኑን አንስተዋል፡፡

የክልሉ መንግስት የህዝቡን ተጠቃሚነት ሊያረጋግጡ የሚችሉ አሰራሮችን በመዘርጋት ባለፉት አመታት ተጨባጭ ለውጦች ማስመዝገቡንም ገልፀዋል፡፡

የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር ከክልሉ ጋር በቅርበት ለመስራት ላሳየዉ ፍላጎትና ድጋፍ ርዕሰ መስተዳድሩ ምስጋናቸዉን አቅርበዋል፡፡

የንግድ ስርዓት ጤናማ መሆን ለሀገር ኢኮኖሚ ማደግ አስተዋጽኦ ከፍተኛ በመሆኑ ይህን ዘርፍ በስኬት ለመምራት በቅንጅት መስራት እንደሚገባም በውይይቱ መጠቀሱን ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

በሚኒስትር ዴኤታ አቶ ፍስሃ ይታገሱ የተመራው ልኡክ በክልሉ በአፍዴራ የጨዉ አምራቾች የሚያከናዉት ስራዎችን ተዘዋውሮ ጎብኝቷል፡፡


አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top