የጊኒ ቢሳው የቀድሞ ፕሬዚዳንት ልጅ በአሜሪካ ከ6 ዓመት በላይ እስር ተፈረደባቸው

30 Days Ago
የጊኒ ቢሳው የቀድሞ ፕሬዚዳንት ልጅ በአሜሪካ ከ6 ዓመት በላይ እስር ተፈረደባቸው
የጊኒ ቢሳው የቀድሞ ፕሬዚዳንት ልጅ በሕገ ወጥ መንገድ አደንዛዥ ዕፅ በማዘዋወር ያገኙትን ገንዘብ፤በሀገራቸው ለተደረገ የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ አውለዋል በሚል በአሜሪካ ፍርድ ቤት ከ6 ዓመት በላይ እስር እንደተፈረደባቸው ተገለጸ።
 
ፍርድ ቤቱ የማላም ባካይ ሳንሃ ልጅ የሆኑት ማላም ባካይ ሳንሃ ጁኒየር፤ ዓለም አቀፍ የሄሮይን ዕፅ ዝውውር ሰንሰለትን ይመሩ እንደነበር መግለጹን ቢቢሲ ዘግቧል።
 
በዚህም ሄሮይን ከተለያዩ ሀገራት ወደ ፖርቹጋል እና ከአውሮፓ ወደ አሜሪካ በማስገባት ወንጀል ክስ ተመስርቶባቸዋል።
 
ሳንሃ ጂኒየር እ.አ.አ በየካቲት ወር 2022 የጊኒ ቢሳው ፕሬዚዳንት ኡማር ሲሶኮ ኢምባሎን በመፈንቅለ መንግስት ለመጣል በተደረገው ያልተሳካ ሙከራ"በግላቸው ተሳትፎ" አድርገዋል ነው የተባለው።
 
በሙከራውም 11 ሰዎች የሞቱ ሲሆን ከነዚህም ውስጥ አብዛኛዎቹ የፀጥታ ኃይሎች ናቸው።
 
ሳንሃ ጁኒየር እ.አ.አ ነሐሴ 2022 በታንዛንያ ከተያዙ ከሳምንታት በኋላ ለአሜሪካ ተላልፈው ተሰጥተዋል።
 
የፍርድ ሂደቱ በ2022 ከተጀመረ በኋላ እ.አ.አ በመስከረም ወር 2023 ወደ አሜሪካ አደንዛዥ ዕፆችን ለማዘዋወር አሲረዋል በሚል በቀረበባቸው ክስ ጥፋተኛ መሆናቸውን አምነዋል።
 
ሳንሃ ጁኒየር የአባታቸው ኢኮኖሚ አማካሪነት ጨምሮ በተለያዩ የስልጣን ተዋረዶች ላይ መስራታቸውን ዘገባው ያመለክታል።
 
አባታቸው ማላም ባካይ ሳንሃ ከእ.አ.አ 2009 ሕይወታቸው እስካለፈበት 2012 ድረስ ጊኒ ቢሳውን በፕሬዚዳንትነት መርተዋል።

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top