በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት በኢትዮጵያ የተሰራው የአረንጓዴ ልማት በልዩነት የሚታይና አስገራሚ ነው፡- ቶኒ ብሌር

7 Mons Ago
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት በኢትዮጵያ የተሰራው የአረንጓዴ ልማት በልዩነት የሚታይና አስገራሚ ነው፡- ቶኒ ብሌር
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አነሳሽነት በኢትዮጵያ የተሰራው የአረንጓዴ ልማት በልዩነት የሚታይና አስገራሚ ነው ሲሉ የቀድሞ የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ቶኒ ብሌር ገለጹ።
 
የቀድሞ የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ቶኒ ብሌር ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጋር በኮፕ28 ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም እና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የምታደርገውን ጥረትና ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳየውን አውደ ርዕይን ጎብኝተዋል።
 
አውደ ርዕዩን ከጎበኙ በኋላም፤"አሁን ላይ ኢትዮጵያ ውስጥ እየታየ ያለው ለውጥ ለማሰብ የሚከብድ ነው" ብለዋል።
 
በግብርናው ዘርፍ እያስመዘገበች ካለው ከፍተኛ እመርታ ባሻገር፤ በአረንጓዴ አሻራ ልማትም የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚያስችል ከፍተኛ ስራ ሰርታለች ሲሉም ገልጸዋል።
 
በዚህም ቀደም ሲል ከውጭ ታስገባቸው የነበሩ እንደ ስንዴ፣ ሩዝ፣ አትክልት እና ፍራፍሬ የመሳሰሉ የግብርና ምርቶች ላይ መሰረታዊ ለውጥ በማምጣት እና ምርትና ምርታማነትን በመሳደግ ወደ ውጭ መላክ የቻለችበትን ስኬት አስመዝግባለች ነው ያሉት።
 
ቶኒ ብሌር አክለውም፤ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማት ላይ የሰራችው አመርቂ ስራ በአፍሪካ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ በልዩነት የሚታይ መሆኑን መጠቆማቸውን የዘገበው ኢዜአ ነው።
 
በኮፕ28 ጉባዔ ላይ ይዛ የቀረበችው አውደ ርዕይም በውጭ ያሉ ማህበረሰቦች የኢትዮጵያ መንግስት በአረንጓዴ ልማት እና የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም ምን አይነት አስደናቂ ስራ እየሰራ እንደሆነ ያሳያል ብለዋል፡፡

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top