እንደ ሀገር የለውጥ ጉዞ ከጀመርን ጊዜ አንስቶ ህብረ ብሔራዊ አንድነቷ የተረጋገጠ ሀገር ለመገንባት ሰፊ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚሚገኙ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር አቶ አዲሱ አረጋ ገለጹ።
“ብዝሃነትና እኩልነት ለሀገራዊ አንድነት” በሚል መሪ ቃል የሚከበረው 18ኛው የብሔር ብሔረሰቦች ቀን በዓል በአምቦ የስልጠና ማዕከል በተለያዩ መርሀ ግብሮች ተከብሯል።
አቶ አዲሱ አረጋ በዓሉን አስመልክቶ በመድረኩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ኢትዮጵያ ማንነቶች እና የብሔራዊ አንድነት ትርክት ተመጣጥነው የተዋቀሩባት ትሆን ዘንድ እየተገነቡ ያሉ አሰባሳቢ ትርክቶች ፍሬ እያፈሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ብዝሀነትን እንደ እድል በመጠቀም፣ የብዝሀነትን ተፈጥሯዊ እና ነባራዊ ሀቅ ሳይክዱ ለሀገር ግንባታ በማዋል፣ነጠላ ትርክቶች የሚፈጥሩትን ጉድለት በአሰባሳቢ ትርክት በመሙላት፣ ታላቁን የብሔራዊነት ትርክት ለመገንባት የተደረጉ ጥረቶችም ሀገራዊ አንድነትን ለማፅናት ተስፋ ሰጪ ውጤቶች እንዳስመዘገቡ ተናግረዋል።
"የሚለያዩንን፣ ቅርበታችንን የሚያርቁ፣ አንድነታችን ላይ የተዛባ ነጠላ አመለካከቶችን የሚተክሉ እሳቤዎችን ከትዉልዱ ላይ በመንቀል ሕብረ-ብሔራዊ አንድነትን በማጎልበት በመደማመጥ ፣ በመከባበር ፣ በመተባበር በመደጋገፍ ላይ የተመሠረተ ታላቁን ትርክት በጋራ ልንገነባ ትውልዳዊ ሀላፊነት ተጥሎብናል" ሲሉም አንስተዋል።
"ለሁላችንም የምትሆን ኢትዮጵያን በመገንባት ሂደት ውስጥ ሁሉም ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ያላቸው አስተዋፆ ጉልህ ነው" ያሉት አቶ አዲሱ፤ የብሔር ብሔረሰቦች በዓል ቀን መከበርም ለዚህ አይተኬ እውነታ እውቅና የሚሰጥ እንደሆነ መግለጻቸውን ከብልጽግና ጽሕፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።