የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም /UNDP/ በኢትዮጵያ ያለውን የሰላም ግንባታ ሂደት ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑን የተቋሙ ዋና ኃላፊ አቺም ሽቴይነር ገለጹ።
በኒው ዮርክ እየተካሄደ በሚገኘው 78ኛው የተመድ ጉባኤ ጎን ለጎን ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን ጋር የተወያዩት አቺም ሽቴይነር፣ UNDP በየትኛውም ሁኔታ እና ጊዜ የረጅም ጊዜ የኢትዮጵያ አጋር መሆኑን ጠቁመዋል።
ከመልሶ ግንባታ እና መልሶ ማቋቋም መርሐ-ግብሮች ባሻገርም ኢትዮጵያ የተያያዘችውን አስደናቂ የዕድገት ግስጋሴዋን ለማስቀጠል ተቋማቸው ድጋፉን እንደሚያደርግም ተናግረዋል።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን በበኩላቸው፣ UNDP እስካሁን ላደረገው ድጋፍ አድንቀው፣ በመንግሥት እና በልማት አጋሮች መካከል የተቀናጀ ጥረት እንዲደረግ ጠይቀዋል።
አቶ ደመቀ በሌሎች የልማት ፕሮግራሞች ላይም ውጤታማ ውይይት ማድረጋቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።