ሶስት የሞስኮ ትምህርት ቤቶች ከሚቀጥለው ሳምንት ጀምሮ አማርኛ እና ስዋሂሊ ቋንቋዎችን ማስተማር ሊጀምሩ ነው

11 Mons Ago
ሶስት የሞስኮ ትምህርት ቤቶች ከሚቀጥለው ሳምንት ጀምሮ አማርኛ እና ስዋሂሊ ቋንቋዎችን ማስተማር ሊጀምሩ ነው

በሩሲያ ዋና ከተማ ሞስኮ የሚገኙ ሶስት ትምህርት ቤቶች በሚቀጥለው ሳምንት በሚጀምረው በአዲሱ የትምህርት ዘመን የአፍሪካ ቋንቋዎችን ማስተማር እንደሚጀምሩ የሞስኮ የትምህርት እና ሳይንስ ዲፓርትመንት አስታውቋል፡፡

ቋንቋውን ለማስተማር የተመረጡት ትምህርት ቤቶች መምህራን ለመማር ማስተማር ስራው ዝግጁ መሆናቸውን የከተማዋ የትምህርት እና ሳይንስ ዲፓርትመንት ጨምሮ ገልጿል፡፡

በሞስኮ የሚገኘው እና መለያው 1522 የሆነ ትምህርት ቤት አማርኛ ቋንቋን ለተማሪዎች እንደሚያስተምር ተገልጿል፡፡

በሌላ በኩል የከተማዋ የፔዳጎጂካል ልቀት ማዕከል እና መለያው 1517 የሆነ ትምህርት ቤት የስዋሂሊ ቋንቋን እንደ ሁለተኛ ቋንቋ እንደሚያስተምር ተጠቅሷል።

የሞስኮ የትምህርት እና ሳይንስ ዲፓርትመንት እንደገለጸው፤ የአፍሪካን ቋንቋዎች በሶስት ትምህርት ቤቶች የማስተማር ዋና ዓለማ ወደፊት ተማሪዎች የአፍሪካ አህጉርን የማጥናት ፍላጎት እንዲያድርባቸው ለማነሳሳት ያለመ ነው፡፡

እንደ ስፑትኒክ ዘገባ የሞስኮ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች እንደ አማርኛ እና ስዋሂሊ ያሉ የውጭ ቋንቋዎችን እንዲማሩ መደረጋቸው የአፍሪካ እና የሩሲያን ወዳጅነት ለማጠናከር እንደሚያግዝም ተመላክቷል፡፡


አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top