ባሳለፍነው ሳምንት ብሪክስ በመባል የሚታወቀው ጥምረት ስድስት አዳዲስ ሀገራትን በአባልነት በመቀበል ታሪካዊ እርምጃ ወስዷል።
ብራዚል፣ ሩሲያ፣ ሕንድ፣ ቻይና እና ደቡብ አፍሪካ የብሪክስ ቡድን ስብስብ ነባር አባላት ሲሆኑ ሳዑዲ ዓረቢያ፣ ኢራን፣ ኢትዮጵያ፣ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ፣ አርጀንቲና እና ግብፅ ብሪክስን እንደ አዲስ ሚቀላቀሉ ሀገራት ናቸው። ነገር ግን እነዚህ ስድስት አዲስ ገቢዎች ብሪክስን ለመቀላቀል ፍላጎት ካላቸው በደርዘን የሚቆጠሩ ሀገራት መካከል የተመረጡ ናቸው።
የጥምረቱ ተጨማሪ መስፋፋት ከG7 ጋር ተቀናቃኝ ለመሆን ስለማሰቡ ብዙዎች ይናገራሉ።
በዓለም የኢየኮኖሚ ውጥረቱ እያየለ ሲሄድ እና ጂኦ-ኢኮኖሚክስ የጦር አውድማ እየሆነ ሲመጣ፣ በደቡቡ የዓለም ክፍል የሚገኙ ሀገሮች ወደ ብሪክስ ቡድን እየተሳቡ የመጡ ይመስላሉ።
በዓለም ኢኮኖሚ ትልቁን ድርሻ የምትይዘው ቻይና የዚህ ጥምረት አንቀሳቃሽ ሞተርም ነች። ታዲያ፣ ለምንድነው ብዙ አገሮች፣ በተለይም የአሜሪካ አጋሮችን ጨምሮ፣ በዚህ ፕሮጀክት ውስጥ የሚሳተፉት እና ተልዕኮውን ለማሳደግ የሚሹት? የሚለው የብዙዎች ጥያቄ ነው።
ብዙዎች ዓለም አሁን ላይ በአዲሱ የቀዝቃዛ ጦርነት ውስጥ ነች ብለው ይከራከራሉ። የዩናይትድ ስቴትስ ኮንግረስ አባላትም ቢሆኑ ነገሩ እውነት ስለመሆኑ ይጠቅሳሉ፤ ሆኖም ይህ ዓነቱ ድምዳሜ ፍፁማዊነት ይጎድለዋል ይላል የኢኮኖሚ ምሁሩ አህማዲ ዓሊ።
እንደ እርሱ ገለጻ፣ አሁን ባለው ዓለም አቀፋዊ የትብብር መልክዓ ምድር በእጅጉ ልዩ የሆነው ነገር ብዙ አገሮች የራሳቸውን አሰላለፍ የመምረጥ አቅም ላይ መሆናቸው ነው።
ምሁራን እና ተንታኞች የደቡቡ የዓለም ክፍል እያደገ መምጣቱን ለብዙ አሥርተ ዓመታት ሲያነሡ ቆይተዋል፤ ለዚህም ከምዕራቡ ዓለም ውጭ ያሉ በርካታ ሀገራት ታይቶ የማይታወቅ እና ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ ዕድገት እንዳስመዘገቡ እና ይህም የዓለምን ኃይል እንደገና እየከፋፈለ መምጣቱን ይጠቅሳሉ።
ይህ አዲስ የብሪክስ ጥምረት በደቡቡ የዓለም ክፍል የሚገኙ ሕዝቦች እና በኃያላን መካከል እያደገ ለመጣው አለመግባባት እንዴት ምላሽ መስጠት እንደሚችሉ እና ሀገሮቻቸውን በታላቅ የሥልጣን ፉክክር ውስጥ እንዴት ማስቀመጥ እንደሚችሉ አማራጮችን ያቀርባል ተብሎም ይጠበቃል።
የጥምረቱ መሥራች ከሆኑት ሀገራት መካከል እነዷ የሆነችው ቻይና በዓለም ላይ ባሉ ትላልቅ ክፍሎች ላይ ኃይልን ለማንሣት እና ለርቀት ወዳጆች የደኅንነት ዋስትና ለመስጠት አሁን ላይ ወታደራዊ አቅሟ አጠራጣሪ ነው።
ስለዚህ አሜሪካ አጋሮቼ ከምትላቸው በአውሮፓ እና በምሥራቅ እስያ የሚገኙ ሀገራት ጋር ያላትን ግንኙነት የሚጎዳ ዓይነት ጥምረትን እምትታገስ አደለችም።
ቤጂንግ ብዙ አጋሮች አሏት፣ እንዲያውም ቤጂንግ ዋሽንግተን ከገነባችው ዓለም አቀፋዊ ሥርዓት ጋርም ያልተጠበቀ ሁሉን አቀፍ ስትራቴጂካዊ ግንኙነት አላት።
ቻይና ስትነሳ፣ ምዕራቡ እና አሜሪካ የገነቧቸው ሕጎች እና በድርጅቶቹ ውስጥ ያለውን የመለኪያ ቅደም ተከተል በተጠንቀቅ ይጠብቃሉ። ቻይና በዓለም አቀፍ መድረኮች ላይ ያላት የድምጽ አሰጣጥ ኃይል እና አቋም አሁንም ከያዘችው ከኢኮኖሚ ክብደት ጋር ሲነጻጸር እጅግ በጣም አናሳ ነው።
ቻይና የድምፅ ኃይሏን እና ሌሎች ታዳጊ ኢኮኖሚዎች ዘመናዊውን ዓለም አቀፋዊ የኢኮኖሚ ስርጭት እንዲወክሉ እና የራሳቸው አስተዋፅኦ እንዲኖራቸው በተደጋጋሚ ጠይቃለች።
ለዛም ነው ብሪክስ ለብዙ የዓለም ደቡብ ክፍል ሀገሮች በእጅጉ ማራኪ እና አጓጊ ጥምረት የሆነው።
የቤጂንግን ከዓለም አቀፉ ሥርዓት ጋር ያላትን ግንኙነት የመረመሩ ምሁራን ቻይና ስለ ምርጫዎቿ ለመሟገት ዓለም አቀፍ ተቋማትን ለማሳተፍ እንደምትፈልግ ይናገራሉ።
አሜሪካ እና የቅርብ አጋሮቿ በአንፃሩ የጋራ እሴቶች እና ጥልቅ ማኅበራዊ መስተጋብር ትስስር እንዲሁም ተመሳሳይ የመንግሥት እና የኢኮኖሚ አስተዳደር ዓይነቶች አሏቸው፤ ይህ አንድ ላይ የሚያቆራኛቸው ሥርዓት የዓለም ጉዳዮችን በሚመለከት በጋራ ተግባር ችግሮችን ይፈታል ብለው ያስባሉ።
በደቡቡ የዓለም ክፍል ያሉ የአሜሪካ አጋሮች ግን በዚህ የአሜሪካ እና ወዳጆቿ ዣንጥላ ስር አይደሉም እና በምትኩ እንደ ብሪክስ ባሉ ፎረሞች በመቀላቀል ከቤጂንግ ጋር የመስማማት ወይም የበለጠ ገለልተኛ ሆነው ለመቆየት አልያም ሁለቱንም ወገኖች ከብሔራዊ ጥቅማቸው ጋር ለማስማማት እንደሚፈልጉ ማረጋገጫ ነው።
ይህ በዓለም የፖለቲካና የኢኮኖሚ መስመር ውስጥ ምን አዲስ ነገር ይዞ እነደሚመጣ አይታወቅም ይላሉ የፖለቲካ ምሁራን ሲል የኢኮኖሚ ምሁሩ አህማዲ ዓሊ በአልጀዚራ ድረ-ገጽ ባሰፈረው ጽሑፉ አመላክቷል።