"የኢትዮጵያ መንግሥት በአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የቀረበበትን የሰብአዊ መብት ጥሰት ክስ በፍፁም አይቀበልም"፦ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር

1 Yr Ago
"የኢትዮጵያ መንግሥት በአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የቀረበበትን የሰብአዊ መብት ጥሰት ክስ በፍፁም አይቀበልም"፦ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር

የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት በሰሜን ኢትዮጵያ በተፈጠረው ጦርነት ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት ተከስቷል ሲል የደረሰበትን ድምዳሜ የኢትዮጵያ መንግሥት በፍፁም እንደማይቀበለው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ።

የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዛሬ ባወጣው መግለጫ፣ የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ጉዳዩን በተመለከተ ያወጣው መግለጫ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን እና የተመድ የሰብአዊ መብት ኮሚሽነር በጋራ ካደረጉት ምርመራ አንፃር ሲታይ ምንም አዲስ ግኝት ያልተካተተበት ነው ብሏል።

በመሆኑም የኢትዮጵያ መንግሥት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ያቀረበበትን ባዶ ውግዘት በፍፁም እንደማይቀበለው ገልጿል።

የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ያወጣው መግለጫ አንድን ወገን ብቻ መወንጀል ላይ ያነጣጠረ መሆኑንም ነው ሚኒስቴሩ በመግለጫ የጠቆመው።

በሌላ በኩል ኢትዮጵያ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አማራጮችን ለመለየት ብሔራዊ ምክክር ለመጀመር በተዘጋጀችበት ወቅት ላይ የወጣ በመሆኑም መግለጫው ወቅቱን ያልጠበቀ ነው ብሎታል።

በተጨማሪም የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ይህን መግለጫ ለማውጣት ያሰበበት ዓላማ ምንም ይሁን ምን መግለጫው በሀገሪቱ አንድን ወገን በሌላኛው ላይ ለማነሣሣት ጥቅም ላይ ሊውል የሚችል ቆስቋሽ መግለጫ ነው ብሏል የኢፌዴሪ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመግለጫው።

ወገንተኛ እና ከፋፋይ የሆነው ይህ የአሜሪካ አካሄድ ሀገሪቱ በኢትዮጵያ አካታች የሰላም ሂደት እንዲረጋገጥ ስታደርገው የቆየችውን ድጋፍ የሚያጨናግፍ ነው ብሏል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመግለጫው።

የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን ጉብኝት ሁለቱ ሀገራት ግንኙነታቸውን ይበልጥ እንደሚያጠናክሩ ተስፋን የፈነጠቀ ነው ያለው መግለጫው፤ በጉብኝቱ ወቅት የተደረገው ግልጽ ውይይት እና የተደረሰበት መግባባት የሁለቱን ሀገራት ስትራቴጂያዊ አጋርነት ለማስቀጠል ይረዳል ብላ ኢትዮጵያ እንደምታምን ገልጿል።

በሽግግር ፍትሕ ላይ ሀገራዊ ምክክር በማካሄድ መግባባት መፍጠርን ጨምሮ ለተበዳዮች ፍትሕን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ሁሉም ዓይነት የተጠያቂነት እርምጃዎች እንደሚወሰዱ ያረጋገጠው መግለጫው፤ የኢትዮጵያ ወዳጆችም ገንቢ ድጋፍ በመለገስ ይህን ሂደት እንዲያግዙ ጥሪ አቅርቧል።


አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top