የኮቪድ- 19ን ለመከላከል የሚያግዝ 30 ሚሊዮን ብር የሚያወጣ 100 ሰው ሰራሽ መተንፈሻ መሳሪያ ድጋፍ መደረጉን ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
ድጋፉን የሞደርን ኢ.ቲ.ኤች አውት ሶርስ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ተወካይ አቶ ታዲዮስ ተፈራ ለጤና ሚኒስትር ዶክተር ሊያ ታደሰ አስረክበዋል፡፡
ድጋፉ በኮሮና ቫይረስ የተጠቁ ዜጎችን ለመርዳት ታስቦ የተደረገ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን በቀጣይም ድጋፉ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገልጿል፡፡
መሳሪያዎቹ በጽኑ ህሙማን ማገገሚያ የሚገኙ ታካሚዎችን ለመርዳት ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርጉ ዶክተር ሊያ ገልጸዋል፡፡
ሚኒስትሯ ማህበሩ በቀጣይ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጠይቀዋል።
የህክምና መሳሪያዎቹን ድጋፍ ያደረጉ እና እቃዎቹን ወደ ሀገር ቤት በማጓጓዝ ያስረከቡ ድርጅቶች ከጤና ሚኒስቴር የምስጋና የምስክር ወረቀት የተሰጣቸው መሆኑን ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡