ሞስኮ "የሽብር ጥቃት" ያለችው የዩክሬን “የሸረሪት ድር ዘመቻ”

11 Days Ago 1292
ሞስኮ "የሽብር ጥቃት" ያለችው የዩክሬን “የሸረሪት ድር ዘመቻ”

 

"ኦፕሬሽን ስፓይደርስ ዌብ" ወይም "የሸረሪት ድር ዘመቻ" የሩሲያን ግዛት በጥልቀት በመዝለቅ በዩክሬን የተፈጸመ የተቀናጀ የድሮን ጥቃት  ነው።

በጥቃቱ በአምስት የጦር አውሮፕላን ማረፊያዎች ላይ የነበሩ እጅግ ዘመናዊ የሩሲያ ቦምብ ጣይና የክትትል አውሮፕላኖችን ወድመዋል።

ዘመቻው በፕሬዚደንት ቮሎዲሚር ዘለንስኪ ክትትል የተደረገበት እንደነበር የዩክሬን የደህንነት አገልግሎት (SBU) ገልጿል።

 

ጥቃቶቹ እንዴት ተፈጸሙ?

ፕሬዚደንት ዘለንስኪ  "ይህ ተልዕኮ ከዕቅድ አንስቶ እስከ ውጤታማ አፈጻጸም ድረስ አንድ ዓመት ከስድስት ወር ከዘጠኝ ቀናት የፈጀ ነው" ሲሉ በኤክስ የማኅበራዊ ትስስር ገጻችው ላይ አስፍረዋል።

ዩክሬን ጥቃቱን ለማቀነባበር በከባድ መኪናዎች ላይ በተገጠሙ የእንጨት ሳጥኖች (ካቢኖች) ውስጥ የተደበቁ ትናንሽ ድሮኖችን ተጠቅማለች።

ከባድ መኪናዎቹ ኢላማቸው ጋር ሲደርሱ፣ ጣሪያዎቹ በርቀት መቆጣጠሪያ አማካኝነት ተከፍተው ድሮኖቹ እንዲበሩ መደረጉን በርካታ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።

በማህበራዊ ሚዲያ የተሰራጩ ቪዲዮዎች ድሮኖቹ ከቆሙ ከባድ መኪናዎች ላይ ሲነሱና በአውሮፕላን ማኮብኮቢያዎች ላይ የነበሩ ትላልቅ አውሮፕላኖችን ሲመቱ ያሳያሉ።

በዘመቻው 117 ድሮኖች ጥቅም ላይ መዋላቸውን፤40 የሩሲያ አውሮፕላኖች መመታታቸውን እና 7 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት የንብረት ውድመት በሩሲያ ላይ መድረሱን ዩክሬን አስታውቃለች።

ይሁንና የዩክሬን የዘርፉ ኤክስፐርቶች ውድመቱ 2 ቢሊዮን ዶላር እንደሚሆን መናገራቸውን ቢቢሲ እና ፎክ ኒውስ ዘግበዋል።

ፕሬዚደንት ዘለንስኪ ዘመቻውን በማዘጋጀት ላይ የተሳተፉ አካላት  ከሩሲያ ግዛት በወቅቱ እንዲወጡ መደረጉን ገልፀው፤  የደህንነት አገልግሎት መሪ የሆኑትን ጄነራል ቫሲል ማሊዩክን አመስግነዋል።

በተጨማሪም የጥቃቱ አንዳንድ ዝርዝሮች ገና ይፋ ሊደረጉ እንደማይችሉ ጠቁመው፤ ነገር ግን "የዩክሬን እርምጃ ያለጥርጥር በታሪክ መዛግብት ውስጥ የሚሰፍር ነው" ብለዋል።