የኤም ፖክስ (የዝንጀሮ ፈንጣጣ) በሽታ በዓለም አቀፈ ደረጃ የህብረተሰብ ጤና ስጋት ተብሎ ተየቀመጠ ቢሆንም በኢትዮጵያ ያለው የስጋት መጠን ዝቅተኛ መሆኑን የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።
የኤም ፖክስ በሽታ ተጠቂ በኢትዮጵያ መመዝገቡን ተከትሎ ባለው ወቅታዊ ሁኔታ የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ ለመገናኛ ብዙኀን ባለሙያዎች ማብራያ ሰጥተዋል።
በኦሮሚያ ክልል ሞያሌ ከተማ አስተዳደር እስካሁን የአንድ ቤተሰብ አባላት የሆኑ ሦስት ሰዎች ላይ በሽታው ተገኝቷል፡፡
ይህንንም ተከትሎ የቅኝት እና የምላሽ ስራዎች በጤና ሚኒስቴር እና ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት እንዲሁም ከክልል ጤና ቢሮዎች ጋር በመሆን እየተሰራ ነው ብለዋል።
በሽታው በንክኪና በመተንፈሻ አካላት ቅርርብ የሚተላለፍ እንደመሆኑ መጠን፣ በሽታው በተገኘበት አካባቢ ከበሽታው ተጠቂዎች ጋር ቅርበት ያላቸው ሰዎች ላይ ምርመራ እየተደረገ መሆኑም ተጠቁሟል።
የበሽታውን ስርጭት ለመቆጣጠርም በየብስ እና በአየር በሚደረጉ ጉዞዎች ላይም ቅኝት እየተደረገ ነው ብለዋል።
አሁን ላይ በሽታው በዓለም አቀፍ ደረጃ ባለፉት አምስት ወራት በ78 በመቶ አድጎል ያሉት ጤና ሚኒስትሯ፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ የቅድመ ዝግጅት እና የምላሽ ስራዎች በቅንጅት እየተሰሩ መሆኑን ተናግረዋል።
የበሽታው ምልክት ሽፍታ፣ ትኩሳት፣ ንፍፊት፣ እብጠት፣ የጡንቻ እና የጀርባ ሕመም በመሆኑ እነዚህን ምልክቶች ያየ ሰው በአፋጣኝ ወደ ጤና ተቋም እንዲቀርብ ተጠይቋል።
አልያም 8335 እና 952 ነፃ የጥሪ አገልሎት እንዲያሳውቅ ተጠይቋል።