የኢትዮጵያ ትንሣኤ ምልክት፦ ጎንደር

22 Days Ago 770
የኢትዮጵያ ትንሣኤ ምልክት፦ ጎንደር

በተለምዶ የፋሲል ግቢ ተብለው የሚታወቁት የጎንደር ቤተ-መንግሥት ሕንጻዎች በኢትዮጵያ ውስጥ ትልቅ ቦታ ከሚሰጣቸው ታሪካዊ ምልክቶች ሲሆኑ፤ የጎንደርን ዘመን ታላቅነት ማሳያ ምስክር ናቸው። እነዚህ የአፄ ሠርፀ ድንግል ቤተ-መንግሥት ከነበረው ጉዛራ የተቀዱ የሚመስሉ ሕንጻዎች የኢትዮጵያ ሥልጣኔ መገለጫዎችም ናቸው።

ስለነዚህ ታሪካዊ ቤተ-መንግሥቶች ሲወሳ በብዙዎቻችን አዕምሮ ውስጥ የሚመላለሰው የአፄ ፋሲል ግንብ ነው። ነገር ግን የአፄ ፋሲል ግንብ፣ የጻድቁ ዮሐንስ ቤተ-መጻሕፍት፣ የጻድቁ ዮሐንስ ግንብ፣ የአፄ ኢያሱ ግንብ፣ የአፄ በካፋ ግንብ፣ የእቴጌ ምንትዋብ ግንብና ቁስቋም ማሪያም ቤተ-ክርስቲያን በግቢው ውስጥ የሚገኙ ናቸው።

ፋሲለደስ፣ ዮሐንስ ቀዳማዊ፣ ኢያሱ ቀዳማዊ፣ ሳልሳዊ ዳዊት፣ በካፋ፣ ኢያሱ ዳግማዊ፣ እቴጌ ምንትዋብ እና ኢዮአስ መዲናቸውን ጎንደር አድርገው ለ200 ዓመታት ኢትዮጵያን የመሩ ነገሥታት ናቸው። እነዚህ ነገሥታት በግቢው ውስጥ የየራሳቸውን ሕንጻ ሠርተዋል።

ፋሲል ግቢ አንኮዬ በር፣ እርግብ በር፣ ባልደራስ በር፣ ወንበር በር፣ ኳሊ በር፣ ራስ በር፣ ፊት በር፣ ግምጃ ቤት፣ ማርያም በር፣ አዛዥ ጠቋሬ በር፣ አደናግር በር፣ እምቢልታ በር እና እልፍኝ በር የሚባሉ በሮች አሉት።

ጎንደር የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ሆና የተመሰረተችው በአፄ ፋሲል አባት አፄ ሱስኒዮስ ቢሆንም፤ በ1628 ዓ.ም በነገሡት ፋሲሊደስ አሁን ያላትን ቅርፅ ይዛ ገናና ሆናለች። ከአክሱም እና ዛግዌ ሥርወ መንግሥታት በኋላ ቋሚ ዋና ከተማ ያልነበራትን የኢትዮጵያን መዲና በጎንደር ያደረጉት አፄ ፋሲል፤ ከተማዋን የፖለቲካ፣ የሃይማኖት እና የባህል ማዕከል አድርገዋታል።