በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያና በጋምቤላ ክልል ከ838 ግራም በላይ የወርቅ ማዕድን ሲያሸሹና ሕገወጥ የጦር መሣሪያ ይዘው የተገኙ ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ሥር ማዋሉን የፀጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ-ኃይል አስታወቀ።
በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ቢሮ ወረዳና በጋምቤላ ክልል ዲማ ወረዳ 20 ክላሽንኮቭ ከ934 መሰል ጥይቶች ጋር፣ 8 ሽጉጥ ከ54 መሰል ጥይቶች ጋር፣ ሁለት ኤፍ ዋን ቦንቦች፣ አንድ GPS፣ 172 የተለያዩ የወርቅ ጌጣጌጥ፣ ከ838 ግራም በላይ የወርቅ ማዕድን፣ 7 የወርቅ ማቅለጫ ማሽኖች፣ 10 የወርቅ ሚዛን፣ ከ1 ሚሊዮን 653 ሺህ ብር በላይ በአሶሳ ዞን ኩምሩክ የፍተሻ ጣቢያ መያዙን የፀጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ-ኃይል ገልጿል።
ተጠርጣሪዎቹ በቁጥጥር ሥር ሊውሉ የቻሉት የፀጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ-ኃይል ከህብረተሰቡ ባገኘው መረጃ መሠረት በአሶሳ ዞን ኩምሩክ የፍተሻ ጣቢያ ባደረገው ፍተሻ መሆኑ ታውቋል።
በመሆኑም ኅብረተሰቡ በመሰል የወንጀል ድርጊቶች የተሰማሩ ግለሰቦችና ቡድኖችን ለፀጥታ አካላት አጋልጦ በመስጠት ኃላፊነቱን እንዲወጣ የፀጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ-ኃይል ጥሪ ማቅረቡን ከፌዴራል ፖሊስ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።