“የወል እውነት እና ሀብት የሆኑትን ሀገር እና ትውልድን ለመገንባት በአረንጓዴ አሻራ መርሐ-ግብር ላይ መሠረት መጣል አስፈላጊ ነው” ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ተናገሩ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ እና ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው ዛሬ ማለዳ ላይ ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት አመራሮች እና ሠራተኞች ጋር በመሆን በየካ ተራራ የአፕል ችግኞችን በመትከል የአረንጓዴ ዐሻራን አስጀምረዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር፣ በዘንድሮው አረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር ችግኞችን ከመትከል ባሻገር ጥራትን ማዕከል ያደረገ ሥራ እንደሚከወን ገልጸዋል።
በዚሁ መሠረት በክረምቱ ወቅት 100 ሺህ የአፕል ችግኞች በጽሕፈት ቤቱ ብቻ የሚተከሉ መሆኑንም ጠቁመዋል።
ዛሬ በየካ ተራራ በተጀመረው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር በአንድ ጀምበር 10 ሺህ የአፕል ችግኝኞች እንደሚተከሉ ተገልጿል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከዚሁ ጋር በተያያዘ በማኅበራዊ ትሥሥር ገጻቸው ባሰፈሩት መልእክት፣ "የጀመርነውን እንጨርሳለን፤ የዘንድሮን የአረንጓዴ ዐሻራ ተከላ ስናገባድድ፣ ኢትዮጵያ 31 ቢሊዮን ችግኞች ትለብሳለች" ብለዋል።
"ኑ! ይህንን ታሪክ አብረን እንሥራ!" ሲሉም ጥሪ አቅርበዋል።
በሮዛ መኮንን